ከጠ/ሚ ዐቢይ የ"አብረን እንሥራ" ጥያቄ የቀረበላቸው ዶ/ር ደሳለኝ ከፖለቲካ ራሳቸውን ማግለላቸውን አስታወቁ

የፎቶው ባለመብት, hopr
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ ከመንግሥታቸው ጋር አብረው እንዲሠሩ ጥሪ ያቀረቡላቸው ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ራሳቸውን ከፖለቲካ ማግለላቸውን አስታወቁ።
ላለፉት አምስት ዓመታት የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄን (አብን) ወክለው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የነበሩት ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ይህንን የገለጹት የምክር ቤቱ የሥራ ዘመን መጨረሻ የሆነውን ስብሰባ ካደረጉ በኋላ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ባጋሩት ጽሑፍ ነው።
በተጨማሪም ግንቦት ወር ላይ በተደረገው ምርጫ ላይ በዕጩነት ቀርበው ቢሆን ኖሮ ብልፅግና ተፎካካሪ ዕጩ ላለማቅረብ ወስኖ እንደነበር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እንደነገሯቸው ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
ደሳለኝ (ዶ/ር) የአማራ ክልል ዋና ከተማ ከሆነችው ባሕር ዳር ተመርጠው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በእንደራሴነት ያሳለፏቸውን አምስት ዓመታት "አስቸጋሪ እና ፈታኝ" ሲሉ ገልጸዋቸዋል።
ባለፉት ስምንት ዓመታት ከፓርቲ ምሥረታ እስከ ከፍተኛ አመራርነት እንዲሁም በምርጫ አሸንፈው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልነት "ድምፅ ለሌላቸው ወገኖቼ እውነተኛ ድምፅ መሆን በመቻሌ የተሰማኝ ክብር እና ኩራት የላቀ ነው" ብለዋል።
547 መቀመጫ ካለው የፌደራል መንግሥቱ ምክር ቤት አባላት መካከል ሞጋች እና ጉልህ ጉዳዮችን በማንሳት የሚታወቁት ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) በሰባተኛው ዙር አጠቃላይ ምርጫ እንደማይሳተፉ ያሳወቁት ከምርጫው ቀደም ብለው ነበር።
ባለፈው ግንቦት ወር በተካሄደው ምርጫ ገዢው ብልጽግና ፓርቲ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በምክር ቤቱ ተሳትፎ እንዲያገኙ በሚል በተወሰኑ የምርጫ ክልሎች ላይ ዕጩዎችን ሳያቀርብ በተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል በተደረገ ፉክክር የተወሰኑ የምክር ቤት መቀመጫዎችን ተቃዋሚዎች አግኝተዋል።
በተለይም የተወሰኑ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች በተሳተፉባቸው የምርጫ ክልሎች ብልጽግና ዕጩ ባለማቅረቡ አሸናፊ ሆነው በቀጣይ ዓመት ሥራውን በሚጀምረው ምክር ቤት ውስጥ ውክልናን ለማግኘት ችለዋል።
የሥራ ጊዜው ማጠናቀቂያ በሆነው እና ማክሰኞ ሰኔ 30/2018 ዓ.ም. በተካሄደው የምክር ቤቱ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ ፓርቲያቸው በምክር ቤቱ ውስጥ ተቃዋሚዎች ውክልና እንዲኖራቸው ወስኖ በምርጫው ላይ መሳተፉን አመልክተዋል።
ለዚህም ብልጽግና ለ85 በመቶ የምክር ቤቱ መቀመጫዎች መወዳደሩን እና በአስራ አምስት በመቶ የምርጫ ክልሎች ላይ ዕጩዎችን አለማቅረቡን ገልጸዋል።
ደሳለኝ ጫኔም ከምክር ቤቱ ስብሰባ በኋላ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ባደረጉት ውይይት "በ7ኛው ዙር ምርጫ በባሕር ዳር ከተማ ለመወዳደር ተመዝግቤ ቢሆን ኖሮ [ብልጽግና] ዕጩ ላለማቅረብ ወስነው እንደነበር ገልጸውልኛል" በማለት በጽሑፋቸው ላይ ጠቅሰዋል።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባዎች ላይ ጠንካራ ጥያቄዎች እና ትችቶችን በመሰንዘር የሚታወቁት ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ግንቦት 24/2018 ዓ.ም. በተካሄደው ምርጫ ላይ እንደማይሳተፉ ያሳወቁት በጥር ወር መጨረሻ ላይ ነበር።
እዚህ ውሳኔ ላይ ካደረሷቸው ምክንያቶች አንዱ "ነፃ፣ ሰላማዊ እና ፍትሐዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ምቹ መደላድል አለመኖሩ" እንደሆነ በወቅቱ አሳውቀው ነበር።
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሊቀ መንበር እና ከፍተኛ አመራር አባል የነበሩት ደሳለኝ (ዶ/ር) በ2013 ዓ.ም. በተካሄደው በስድስተኛው አጠቃላይ ምርጫ የባሕር ዳር ከተማን ወክለው ምርጫ አሸንፈው ነበር የሕዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት አባል የነበሩት።
ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) በሕዝብ ዘንድ ዕውቅናቸው የጨመረው በምክር ቤት ውስጥ በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚገኙበት ጊዜ በሚያነሷቸው ጥያቄዎች እና በሚሰነዝሯቸው አስተያየቶች የተነሳ ነው።
እንደራሴው የምክር ቤት አባል ሳሉ ጥር 22/2016 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች ከቤታቸው ተይዘው ተወስደው ለአንድ ወር ተኩል በእስር ላይ የቆዩ ሲሆን፣ ስለታሰሩበት ጉዳይ እስካሁን ያሉት ነገር የለም።
ነገር ግን አሁን የምክር ቤት አባልነታቸው መጠናቀቁን በተመለከተ ባስተላለፉት መልዕክት ለደጋፊዎቻቸው ምሥጋና ሲያቀርቡ "በተለይም ከሁለት ዓመት ከመንፈቅ በፊት ለ45 ቀናት በታሰርኩበት ወቅት በጸሎትና በሐሳብ ያገዛችሁኝ ውድ ወገኖቼ፣ የለገሳችሁኝ ፍቅር ጉልበት ሆኖኝ ዛሬ በኩራትና በነጻ ሕሊና የሕዝብ አገልግሎቴን እንድፈጽም አድርጎኛል" ብለዋል።
የዩኒቨርሲቲ መምህር የነበሩት ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በተሰናባቹ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ አገራቸውን ማገልገላቸውን እንዲቀጥሉ እና "አብረን እንሥራ በማለት ላቀረቡልን ጥሪና ላሳዩን አክብሮት ከልብ የመነጨ ምስጋናዬን አቀርባለሁ" ብለዋል።
ደሳለኝ (ዶ/ር) በመልዕክታቸው ከምክር ቤት አባልነት ከተሰናበቱ በኋላ ራሳቸውን ከማንኛውም ቀጥተኛ የፖለቲካ እንቅስቃሴ" እንደሚያገሉ እና "ለጊዜው በማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ውስጥ በአባልነትም ሆነ በደጋፊነት እንደማይሳተፉ አሳውቀዋል።
በተጨማሪም በመጪው በሙያቸው አገራቸውን ለማገልገል እና ጎን ለጎን ደግሞ ወደ ግሉ ሴክተር በመግባት በሚያስቧቸው የሥራ ውጥኖች ላይ ለመሰማራት እና ለቤተሰባቸው በቂ ጊዜ መስጠት ዕቅዳቸው መሆኑን አመልክተዋል።
ጨምረውም "ፖለቲካዊ ተሳትፎዬ ቢያበቃም የአማራን ሕዝብ አንድነት በሚያጠናክሩ፣ የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ወንድሞቹ ጋር ያለውን አብሮነትና መስተጋብር በሚያሳድጉ እንዲሁም የኢትዮጵያውያንን ኑሮ በሚያሻሽሉ ማኅበራዊ እና አገራዊ ጉዳዮች ላይ በሙያዬ ማድረግ የምችለውን አስተዋጽኦ ሁሉ አደርጋለሁ" ብለዋል።















