የደቡብ አፍሪካ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪው ጁሊየስ ማሌማ ሽጉጥ በመተኮስ አምስት ዓመት እስራት ተፈረደባቸው

የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

የ45 ዓመቱ የደቡብ አፍሪካው ተቃዋሚ ፖለቲከኛ ጁሊየስ ማሌማ ሕገወጥ ሽጉጥ ታጥቆ በሕዝብ ፊት በመተኮስ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘታቸው የአምስት ዓመታት እስር ተፈረደባቸው።

ዳኛ ትዋኔት ኦሊቪየር የኢኮኖሚክ ፍሪደም ፋይተርስ ፓርቲ መሪ እና የፓርላማ አባል የሆኑት ማሌማ ይግባኝ እንዲሉ በመፍቀዳቸው በቀጥታ ወደ እስር ቤት አልተወሰዱም።

ጥቁር ሙሉ ልብስ እና ቀይ ከረባት ለብሰው ፍርድ ቤት የተገኙት ማሌማ የፖለቲካ የወደፊት ዕጣ ፈንታቸውን አደጋ ላይ የሚጥል ቢሆንም ኦሊቪየር ቅጣቱን ሲያነቡ ፊታቸው ላይ የስሜት መቀያየር ብዙም አልተነበበም።

ባለፈው ዓመት ሕገወጥ የጦር መሳሪያ መያዝ፣ በሕዝብ ፊት መተኮስ እና የግድየለሽነት አደጋን ጨምሮ በአምስት ጥፋቶች ተፈርዶባቸዋል።

ፍርዱ ከጸና ማሌማ ለአምስት ዓመታት የፓርላማ አባል ከመሆን ይታገዳሉ።

የፖለቲካ ተንታኝ ሳንዲሌ ስዋና ለቢቢሲ እንደተናገሩት የይግባኝ ሂደቱ በርካታ ዓመታት ሊወስድ ስለሚችል የፓርቲው መሪ የፖለቲካ ሥራቸውን መቀጠል ይችላሉ።

ክሱ የተመሰረተው በ2018 ማሌማ በአገሪቱ ምሥራቅ ኬፕ ግዛት በተካሄደ የፓርቲው አምስተኛ ዓመት ክብረ በዓል ወቅት ከፊል አውቶማቲክ ጠመንጃ ወደ አየር ላይ ሲተኩሱ የሚያሳይ ቪዲዮ ከወጣበት ክስተት ጋር በተያያዘ ነው።

በኩጎምፖ ከተማ ለተሰየመው ችሎት ማሌማ የተኮሱት በዓሉን ለማክበር እንደሆነ ተናግረዋል።

ኦሊቨር ውሳኔ ሲሰጡ ግን "ይህ... ድንገተኛ ድርጊት አልነበረም። የምሽቱ ክስተት ነበር" ማለታቸውን የኤኤፍፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።

የፖለቲካ አቋማቸው በውሳኔው ላይ ምንም ተጽዕኖ ባይኖረውም፣ በደቡብ አፍሪካ ብዙ ተከታዮች ያሏቸው በመሆኑ ለድርጊታቸው ተጠያቂ መሆን እንዳለባቸው አክለዋል።

ከችሎት ውጭ ላሉ ደጋፊዎቹ በኦሊቪየር ላይ ተከታታይ ማስረጃ የሌላቸውን ክሶች አቅርበዋል። ቀጥተኛ ማስረጃ ሳያቀርቡም የጥፋተኝነት ውሳኔው እና ቅጣቱ የሴራ ውጤት መሆኑን ተናግረዋል።

"ይህን ድምጽ ለማፈን በሁሉ መንገድ እየሞከሩ ነው። በፍጹም አያሸንፉም" ማለታቸውን ኤኤፍፒ ዘግቧል። "ከጠላት ጋር እየተዋጋን ነው፤ ጠላት ደግሞ የነጭ የበላይነት ነው" ብለዋል።

ማሌማ ደፋር፣ ግርማ ሞገስ ያላቸው እና አክራሪ የግራ ክንፍ ፖለቲከኛ በመሆን ትልቅ ስም ያላቸው ሲሆን ታማኝ ደጋፊዎችም አሏቸው።

በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ማሌማን በዜማዎች እና በአብዮታዊ ዘፈኖች ደግፈዋቸዋል።

ይግባኝ እንዲሉ እንደሚፈቀድላቸው የሚገልጸው ዜና ሲሰማ በጦሳ ቋንቋ "ሲጎዱካ ናዬ" ብለው መጮህ ጀምረዋል። ይህም "ዛሬ ከእሱ ጋር እንሄዳለን" እንደማለት ነው።

ማሌማ በአንድ ወቅት የአፍሪካ ብሔራዊ ኮንግረስ የወጣቶች ክንፍ መሪ ነበሩ። ከወቅቱ ፕሬዝዳንት ጃኮብ ዙማ ጋር በተፈጠረ አለመግባባት ከፓርቲው ከተባረሩ በኋላ ፓርቲውን አቋቁመዋል።

ማሌማ በነጮች የተያዘ መሬት እንዲወረስ ባቀረቡት ጥሪ እና ሐብትን ለጥቁሮች ለማስተላለፍ የበለጠ መሠራት እንዳለበት በመከራከር ፓርቲያቸው የኤኤንሲንት ድምጽ እየወሰደ ይገኛል። በ2024 ምርጫ የአገሪቱ አራተኛው ትልቁ ፓርቲ ለመሆን በቅቷል።

ማሌማ ባለፈው ጥቅምት ወር ጥፋተኛ መባላቸውን ተከትሎ ከፍርድ ቤቱ ውጭ ላሉ ሰዎች "ወደ እስር ቤት መሄድ ወይም ሞት የክብር ምልክት ነው" በማለት እንደተናገሩ ተጠቅሷል።

"ለአብዮቱ መታሰርን [ወይም] መሞትን አንፈራም። የፈለጉትን ማድረግ ቢፈልጉም ፈጽሞ እንደማንሸሽግ ማወቅ አለባቸው።"

በተጨማሪም እስከ ደቡብ አፍሪካ ሕገ መንግሥታዊ ፍርድ ቤት ድረስ ይግባኙን እንደሚያቀርቡ ቃል ገብተዋል።

የ10 ፓርቲ ጥምረት መንግሥት የሚመራው የኤኤንሲ ዋና ጸሐፊ በማሌማ ላይ በተላለፈው ውሳኔ ማዘኑን ገልጸዋል።

"እዚህ ላይ በዘረኛው አፍሪፎርም የሚነገረን ዋና መልዕክት ለጥቁር ሕዝቦች የምንቆም ከሆነ፣ ለተገለሉት ሰዎች የምንቆም ከሆነ እና ለትውልድ ተልዕኳችን የምንቆም ከሆነ ዒላማ እንሆናለን" ሲሉ ፊኪሌ ምባሉላ ሐሙስ ዕለት ከፍርዱ በኋላ በኤክስ ላይ ጽፈዋል።

አፍሪፎርም ቀደም ሲል ሁሉንም ዓይነት የዘረኝነት ዓይነቶች እንደሚያወግዝ አስታውቋል። ቃል አቀባዩም ይህ ጉዳይ ስለ ዘር ሳይሆን "ስለግድየለሽ እና ሕገ-ወጥ ድርጊቶች" እንደሆነ ተናግረዋል።

ድርጅቱ በማሌማ ላይ በተፈረደበት ሌላ ክስ ውስጥም ሚና ነበረው።

ባለፈው ነሐሴ ወር በ2022 ሰልፍ ላይ ባደረገው ንግግር ምክንያት በጥላቻ ንግግር ጥፋተኛ ተብሏል።

አንድ ነጭ ግለሰብ የፓርቲው አባል ላይ ጥቃት የሰነዘረበትን ክስተት ተከትሎ ማሌማ "ማንም ነጭ ሰው አይደበድበኝም... ለመግደል ፈጽሞ መፍራት የለብህም። አብዮት በአንድ ወቅት ግድያ እንዲኖር ይጠይቃል" ብለዋል።

ፍርድ ቤቱ እነዚህ አስተያየቶች "ጉዳት የማነሳሳት ዓላማ እንዳላቸው አሳይተዋል" ሲል ቢወስንም ግን ፓርቲው ከአውድ ውጭ እንደተወሰደ ተናግሯል።

ማሌማ በፖለቲካ ሰልፎች ላይ "ቦየርን (አፍሪካነር) ላይ ተኩስበት፤ ገበሬው ላይ ተኩስበት" የሚሉትን ቃላት የያዘ ዘፈን በመዘፈናቸውም ተተችተዋል።

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ግንቦት ወር ከደቡብ አፍሪካ አቻቸው ሲሪል ራማፎሳ ጋር ባደረጉት የዋይት ሐውስ ስብሰባ ላይ ይህንን አንስተው ጉዳዩን ውጥረት የተሞላበት እንዲሆን አድርገዋል።