ቻይና ለኢራን የጦር መሣሪያ ሸጣለች መባሉን አስተባበለች

የፎቶው ባለመብት, Reuters
ቻይና ለኢራን የጦር መሣሪያ አቅርባለች ወይንም ለማቅረብ ታስባለች የሚለው ውንጀላ መሠረተ ቢስ ነው ስትል አጣጣለች።
ሰኞ ዕለት ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አገራቸው ለኢራን የጦር መሣሪያ አቅርባለች ወይም ለማቅረብ አቅዳ ነበር የሚለውን ዘገባ “መሠረተ ቢስ ውንጀላ” ሲሉ አጣጥለውታል።
የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን የደህንነት ምንጮችን በመጥቀስ ቻይና ለኢራን የጦር መሣሪያ ታቀርባለች ሲሉ መዘገባቸውን ተከትሎ ስጋት ተፈጥሯል።
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ቤይጂንግ ለቴህራን ወታደራዊ ድጋፍ አድርጋለች በሚል 50 በመቶ አዲስ ታሪፍ እንደሚጣልባት ዝተው ነበር።
ቻይና የፕሬዚዳንቱን ውንጀላ ያስተባበለችው ሲኤንኤን ሦስት የአሜሪካ የደህንነት ምንጭ ጠቅሶ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ለኢራን አዲስ የአየር መቃወሚያ ስርዓት ልታቀርብ ነው ሲል መዘገቡን ተከትሎ ነው።
በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ዘ ኒውዮርክ ታይምስ እንዲሁ የአሜሪካ ባለሥልጣናትን ጠቅሶ ቤጂንግ ትከሻ ላይ ተደርጎ የሚተኮስ ሚሳዔል ሳትልክ አትቀርም ብሏል።
ቻይና እነዚህን ዘገባዎች በማስተባበል "ወታደራዊ ቁሳቁሶች ወደ ሌሎች አገራት በሚላክበት ወቅት የአገሪቱን የውጭ ንግድ ቁጥጥር ሕጎች እና ደንቦች እንዲሁም በዓለም አቀፍ ግዴታዎች መሠረት ጥብቅ ቁጥጥሮችን በመተግበር ሁልጊዜ ጥንቃቄ እና ኃላፊነት የተሞላበት እርምጃ እንወስዳለን” ብላለች።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጉኦ ጂያኩን “መሠረተ ቢስ ውንጀላዎችን ወይም ይሁነኝ ተብለው የሚደረጉ ማዛመዶችን እንቃወማለን” ሲሉ በዕለታዊ ጋዜጣዊ መግለጫቸው ወቅት ተናግረዋል።










