በሊባኖስ የተኩስ አቁም ቢደረግም የሰዎችን ሕይወት የቀጠፉ ክስተቶች እየተመዘገቡ ነው

የፎቶው ባለመብት, Reuters
አሜሪካ እና ኢራን የገቡትም ሆነ እስራኤል እና ሊባኖስ የደረሱበት የተኩስ አቁም ስምምነት እየተከበረ ይመስለል። ሊባኖስ ውስጥ ግን ለሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት የሆኑ ክስተቶች ተፈጥረዋል።
ተኩስ አቁሙ ተግባራዊ መሆን ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ ሁለት ወታደሮች መሞታቸውን የእስእራኤል መከለከያ ሠራዊት ገልጿል።
የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያመለክተው አንዱ ወታደር ሕይወቱ ያለፈው ሕንጻዎች በሚያጸዱበት ሰዓት በደረሰ ፍንዳታ ነው። በዚህ ክስተት ሌሎች ሦስት ሰዎች ቆስለዋል።
ሌላኛው የእስራኤል ወታደር በተገደለበት ክስተት ደግሞ ዘጠኝ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውን የእስራኤል ጦር አስታውቋል።
የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያመለክተው፤ ወታደሮቹ የነበሩበት መሣሪያ የታጠቀ ተሽከርካሪ በሚጓዝበት ወቅት የተቀበረ ፈንጂ ረግጧል። እስራኤል ፈንጂው መቼ እንደተቀበረ እና የተኩስ አቁም ስምምነቱ ጥሰት ይሆን እንደሆነ ለማረጋገጥ ምርመራ እንደምታካሂድ ተዘግቧል።
በሌላ ክስተት ደግሞ የተባበሩት መንግሥታት የሊባኖስ ጊዜያዊ ኃይል አባል የሆነ ፈረንሳዊ ሰላም አስከባሪ ሊባኖስ ውስጥ ተገድሏል። የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ለጥቃቱ ሄዝቦላህን ተጠያቂ ያደረጉ ሲሆን ታጣቂ ቡድኑ ግን ከክስተቱ ጋር “ምንም ግንኙነት እንደሌለው” በመግለጽ አስተባብሏል።




















