ቀጥታ, የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ የዘጋችው ኢራን የሰላም ስምምነት ላይ የመድረስ ጉዳይ “ሩቅ” መሆኑን ገለጸች

የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ሞሐማድ ባገር ጋሊባፍ ከአሜሪካ ጋር የሚካሄደውን ጦርነት ለመቋጨት በሚደረገው ድርድር “መሻሻሎች ቢመዘገቡም” ሁለቱ ወገኖች “ለመጨረሻ ውይይት ሩቅ” መሆናቸውን ተናገሩ። የኢራኑ ፓርላማ አፈ ጉባኤ ጋሊባፍ ትናንት በመንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ በተላለፈ ንግግራቸው አሜሪካ የጣለችውን እግድ “የተሳሳተ ግምገማ እና ውሳኔ” ሲሉ ጠርተውታል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በሊባኖስ የተኩስ አቁም ቢደረግም የሰዎችን ሕይወት የቀጠፉ ክስተቶች እየተመዘገቡ ነው

    ታንክ ላይ የቆሙ የእስራኤል ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    አሜሪካ እና ኢራን የገቡትም ሆነ እስራኤል እና ሊባኖስ የደረሱበት የተኩስ አቁም ስምምነት እየተከበረ ይመስለል። ሊባኖስ ውስጥ ግን ለሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት የሆኑ ክስተቶች ተፈጥረዋል።

    ተኩስ አቁሙ ተግባራዊ መሆን ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ ሁለት ወታደሮች መሞታቸውን የእስእራኤል መከለከያ ሠራዊት ገልጿል።

    የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያመለክተው አንዱ ወታደር ሕይወቱ ያለፈው ሕንጻዎች በሚያጸዱበት ሰዓት በደረሰ ፍንዳታ ነው። በዚህ ክስተት ሌሎች ሦስት ሰዎች ቆስለዋል።

    ሌላኛው የእስራኤል ወታደር በተገደለበት ክስተት ደግሞ ዘጠኝ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውን የእስራኤል ጦር አስታውቋል።

    የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘገባ እንደሚያመለክተው፤ ወታደሮቹ የነበሩበት መሣሪያ የታጠቀ ተሽከርካሪ በሚጓዝበት ወቅት የተቀበረ ፈንጂ ረግጧል። እስራኤል ፈንጂው መቼ እንደተቀበረ እና የተኩስ አቁም ስምምነቱ ጥሰት ይሆን እንደሆነ ለማረጋገጥ ምርመራ እንደምታካሂድ ተዘግቧል።

    በሌላ ክስተት ደግሞ የተባበሩት መንግሥታት የሊባኖስ ጊዜያዊ ኃይል አባል የሆነ ፈረንሳዊ ሰላም አስከባሪ ሊባኖስ ውስጥ ተገድሏል። የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ለጥቃቱ ሄዝቦላህን ተጠያቂ ያደረጉ ሲሆን ታጣቂ ቡድኑ ግን ከክስተቱ ጋር “ምንም ግንኙነት እንደሌለው” በመግለጽ አስተባብሏል።

  2. ኢራን ከአሜሪካ ጋር ቀጣይ ዙር ድርድር ለማድረግ የተቀመጠ ቀን እንደሌለ ገለጸች

    የኢራንን ባንዲራ የያዘች ሴት

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty Images

    ኢራን እና አሜሪካ ለሚያደርጉት ቀጣይ ዙር ድርድር የተቆረጠ ቀን አለመቀመጡን እና ከንግግሩ በፊት የመግባቢያ ማዕቀፍ ላይ ስምምነት ሊደረስ እንደሚገባ የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ።

    በአውሮፓውያኑ 1979 የኢራን እስላማዊው አብዮት ከፈነዳ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ፓኪስታን ውስጥ የተደረገው የባለፈው ሳምንት የአሜሪካ እና ኢራን ንግግር ያለ ስምምነት መቋጨቱ ይታወሳል።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በዚህ ሳምንት መጨረሻ ቀጥተኛ ንግግር ሊደረግ እንደሚችል ለሮይተርስ ተናግረው ነበር።

    ዲፕሎማቶች ግን ንግግሩ ይካሄዳል ተብሎ የሚጠበቅባት የፓኪስታን ዋና ከተማ ኢስላማድ ውስጥ ድርድር ለማድረግ ከሚያስፈልገው ሎጂስቲክስ አንጻር የመደረግ እድሉ ዝቅተኛ እንደሆነ ለዜና ወኪሉ ተናግረዋል።

    ቱርክ ውስጥ እየተካሄደ ባለ የዲፕሎማሲ ፎረም ላይ እየተሳተፉ ያሉት የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳኢድ ኻቲብዛዴህ ከዝግጀቱ ጎን ለጎን ከጋዜጠኞች ጋር ቆይታ አድርገው ነበር።

    "አሁን ትኩረታችን በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለውን የመግባቢያ ማዕቀፍ ማጠናቀቅ ላይ ነው። ከጅምሩ እንዲከሽፍ ወደተፈረደበት እና ለሌላ ዙር ግጭት ምክንያት ሊሆን ወደሚችል ማንኛውም ድርድር ወይም ስብሰባ መግባት አንፈልግም" ማለታቸውን ዘገባው አመልክቷል።

    “ማዕቀፉ ላይ እስካልተስማማን ድረስ ቀኑን ማስቀመጥ አንችልም” ያሉት ሳኢድ፤ ከዚህ ቀደም በተደረገው ንግግር ውጤት ላይ ያልተደረሰው አሜሪካ የኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ ባቀረበችው ጥያቄ ምክንያት መሆኑን ጠቁመዋል።

    በድርድሩ “ከፍተኛ መሻሻል ታይቶ ነበር። ነገር ግን ሌላኛው ወገን ኢራንን ከዓለም አቀፍ ሕግ ውጪ ለማድረግ በመሞከር የተከተለው ሁሉንም ማግኘት አለብኝ የሚል አካሄድ ስምምነት ላይ ከመድረስ አግዶናል” ብለዋል።

  3. የፈረንሳይ ሰላም አስከባሪ ወታደር ሊባኖስ ውስጥ ተገደለ

    የተመድ ሰላም አስከባሪ ተሽከርካሪ እና ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የተባበሩት መንግሥታት ሰላም አስከባሪ ኃይል ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ በተከፈተበት ጥቃት አንድ ፈረንሳዊ ወታደር ሲገደል፤ ሦስት ሰዎች ቆሰሉ። ባለሥልጣናት ጥቃቱ የተፈጸመው ሆነ ተብሎ እንደሆነ በመግለጽ ከስሰዋል።

    ፈረንሳዊው ወታደር ሲያገለግልበት የነበረው የተባበሩት መንግሥታት የሊባኖስ ጊዜያዊ ኃይል፤ የሰላም አስከባሪ አባሉ መገደሉን አረጋግጧል። የሰላም አስከባሪው ኃይል ተሽከርካሪ በተከፈተበት ተኩስ ከቆሰሉት ሦስት ሰዎች መካከል ሁለቱ የደረሰባቸው ጉዳት ከፍተኛ እንደሆነ ተገልጿል።

    የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ለተፈጸመው ጥቃት ሄዝቦላህን ተጠያቂ አድርገዋል። በኢራን የሚደገፈው ታጣቂ ቡድን በበኩሉ ከክስተቱ ጋር “ምንም አይነት ግንኙነት” እንደሌለው በመግለጽ አስተባብሏል።

    ሄዝቦላህ ባወጣው መግለጫ የቀረበበትን ውንጀላ “የተጣደፈ” እና “መሠረት የለሽ ክስ” ሲል ጠርቶታል። “የሊባኖስ ጦር ምርመራ ሙሉ ሁኔታውን እስከሚገልጽ ድረስ ክስተቱን በተመለከተ የሚደረግ ፍርድ ማስተላለፍ እና ተጠያቂነት መስጠት ላይ” ጥንቃቄ እንዲወሰድ ጠይቋል።

    በደቡባዊ ሊባኖስ ይህ ጥቃት የተፈጸመው በሄዝቦላህ እና እስራኤል መካከል ባገረሸው ግጭት የተነሳ የሰላም አስከባሪ አባላት ላይ የተጋረጠው ስጋት በጨመረበት ሰዓት ነው።

    እስራኤል እና ሊባኖስ የደረሱት የ10 ቀናት የተኩስ አቁም ተግባራዊ መሆን የጀመረ ሲሆን ስምምነቱን ይፋ ያደረገችው አሜሪካ ሄዝቦላህ ለተኩስ አቁሙ እንዲገዛ እያሳሰበች ነው።

    የፈረንሳዩ ፕሬዝዳን ማክሮን “ሁሉም ነገር የሚጠቁመው የጥቃቱ ኃላፊነት ሄዝቦላህ ላይ እንደሚወድቅ ነው” ብለዋል። የሊባኖስ ባለሥልጣናት “በአስቸኳይ ጥቃት ፈጻሚዎቹን በቁጥጥር ስር እንዲያውሉ” ጠይቀዋል።

    የተመድ ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ቃል አቀባይም ጥቃቱን አውግዘዋል። ሰላም አስከባሪ ኃይሉ ተኩስ የተከፈተበት የሄዝቦላህ አባላት እንደሆነ በተገመቱ “መንግሥታዊ ያልሆኑ አካላት” መሆኑን ተናግተዋል።

    ሁሉም አካላት የተኩስ አቁሙን እንዲያከብሩ እና ግጭቶችን እንዲያቆሙም አሳስበዋል።

    የሊባኖስ ጦር ኃይል በበኩሉ ከታጠቁ ግለሰቦች ጋር የተኩስ ልውውጥ እንደተካሄደ ገልጿል። አገሪቱ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን ከፕሬዝዳንት ማክሮን ጋር በደረጉት ስልክ ንግግር ጥቃቱን አውግዘዋል፤ ተጠያቂዎቹ አካላት ለፍትሕ እንደሚቀርቡም ገልጸዋል።

  4. የቀድሞ የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ካማላ ሃሪስ ትራምፕ ወደ ጦርነት “ተጎትተው” የገቡት በኔታንያሁ ነው አሉ

    የቀድሞ ምክትል ፕሬዝዳንት ካማላ ሃሪስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቀድሞ ምክትል ፕሬዝዳንት ካማላ ሃሪስ፤ ዶናልድ ትራምፕ በእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ “ተጎትተው” ከኢራን ጋር የሚደረገው ጦርነት ውስጥ ገብተዋል ሲሉ ተናገሩ።

    ካማላ ይህንን አስተያየታቸውን ያሰሙት ትናንት ቅዳሜ በተካሄደ አንድ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ላይ ባደረጉት ንግግር ነው።

    “ወደ ጦርነት ገብቷል፤ የገባውም በቢቢ ኔታንያሁ ተጎትቶ ነው፤ ስለዚህ ጉዳይ ግልጽ መሆን አለብን። አሜሪካውያን የማይፈልጉት ጦርነት ውስጥ ነው የገባው፣ የአሜሪካ የሠራዊት አባላትን ሕይወት አደጋ ላይ ጥሏል” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለካማላ ሃሪስ ንግግር በቀጥታ ምላሽ ባይሰጡም እስራኤል “ታላቅ አጋር” መሆኗን የሚገልጽ ጽሑፍ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አጋርተዋል።

    “ሰዎች እስራኤልን ወደዱም አልወደዱ የዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ታላቅ አጋር መሆኗን አስመስክራለች። ደፋር፣ ቆራጥ፣ ታማኝ እና ብልህ ናቸው” ሲሉ አወድሰዋል።

    ትራምፕ አክለውም፤ “በግጭት እና ውጥረት ሰዓት ላይ ከሌሎች በተቃራኒ እውነተኛ ቀለማቸውን አሳይተዋል። እስራኤል በጥንካሬ ትዋጋለች፤ እንዴት እንደምታሸንፍም ታውቃለች” ብለዋል።

  5. የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ የዘጋችው ኢራን የሰላም ስምምነት ላይ የመድረስ ጉዳይ “ሩቅ” መሆኑን ገለጸች

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ሞሐማድ ባገር ጋሊባፍ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ሞሐማድ ባገር ጋሊባፍ ከአሜሪካ ጋር የሚካሄደውን ጦርነት ለመቋጨት በሚደረገው ድርድር “መሻሻሎች ቢመዘገቡም” ሁለቱ ወገኖች “ለመጨረሻ ውይይት ሩቅ” መሆናቸውን ተናገሩ።

    የኢራንን ተደራዳሪ ቡድን የመሩት ጋሊባፍ ባለፈው ሳምንት በፓኪስታን ተገኝተው ከምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስን እና ሌሎች የአሜሪካ ልዑካን ጋር ንግግር አድርገው ነበር። ይህ ንግግር ያለ ስምምነት የተቋጨ ሲሆን ቀጣዩ ዙር ድርድር መቼ እንደሚካሄድ እስካሁን ቁርጥ ቀን አልተቀመጠም።

    ከዚህ ንግግር በኋላ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎችን አግደዋል። ኢራን ከጦርነቱ መጀመር ወዲህ ዘግታው የቆየችውን ወሳኙን የባሕር መተላላፊያ ከከፈተች በኋላም የአሜሪካ እግድ ጸንቶ እንደሚቆይ ትራምፕ ተናግረዋል።

    በዚህ ያልተደሰተችው ኢራን ትናንት በድጋሚ ወሽመጡን ዘግታለች።

    የኢራኑ ፓርላማ አፈ ጉባኤ ጋሊባፍ ትናንት በመንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ በተላለፈ ንግግራቸው አሜሪካ የጣለችውን እግድ “የተሳሳተ ግምገማ እና ውሳኔ” ሲሉ ጠርተውታል።

    "እገዳውን የማያነሱ ከሆነ በወሽመጡ በኩል የሚደረግ ጉዞ በእርግጠኝነት እንደሚገደብ ተናግሬ ነበር" ብለዋል። አሁንም ቢሆን ወሽመጡ በኢራን “ቁጥጥር ስር” እንደሚገኝ ተናግረዋል።

    “ለሁለት ወይም ሦስት ቀናት ያህል [አሜሪካ] ሆነ ብላ ከበባ ፈጽማለች። ከበባ ምን ማለት ነው? ሁሉም ሰው ይመጣል፣ ይሄዳል፤ ኢራን ግን አትጓዝም ማለት ነው። እንዴት ያለ የሞኝ እና የድንቁርና ውሳኔ ነው” ሲሉ በጠንካራ ቃላት ተችተዋል።

    አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የተጠመዱ ፈንጂዎችን የማጽዳት ዘመቻ ማካሄድ እንደምትፈልግ የተናገሩት ጋሊባፍ፤ ኢራን "በጽናት በመቆም አሜሪካን ተጋፍጣለች" ብለዋል።

    "ይህንን እቅድ እንደ የተኩስ አቁም ስምምነት ጥሰት ነው የቆጠርነው፤ እንዲህ አይነት እርምጃ የሚወስዱ ከሆነም ጥቃት እንደምንፈጽም ተናግረናል" ሲሉ አቋማቸውን ግልጽ አድርገዋል።

    ጋሊባፍ፤ ጦርነቱ ከተጀመረ ወዲህ ከኢራን መንግሥት ውስጥ መዋቅር ውስጥ ቁልፍ ሰው ሆነው የወጡ ፖለቲከኛ ናቸው። ባለፈው ሳምንት ኢራን እና አሜሪካ በኢስላማባድ ባደረጉት ንግግር ላይም የቴህራንን ልዑክ መርተዋል።

  6. ትራምፕ ኢራን “ልታስፈራራን አትችልም” አሉ

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ የኢራን ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግመኛ መዝጋቱን ካስታወቀ በኋላ በሰጡት ምላሽ ቴህራን “ልታስፈራራን አትችልም” አሉ።

    “ለረዥም ዓመታት እንዳደረጉት የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመዝጋት ይፈልጋሉ” ሲሉ ለጋዜጠኞች የተናገሩት ትራምፕ “ሊያስፈራሩን አይችሉም” ብለዋል።

    ትራምፕ ከኢራን ጋር “በጣም ጥሩ ውይይት እየተካሄደ ነው” በማለት ቴህራን “ላለፉት 47 ዓመታት እንደነበሩት ለማታለል እየሞከሩ ነው” ብለዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመዝጋት ይፈልጋሉ ያሉት ትራምፕ፣ አሜሪካን “እንድታስፈራራ” አንፈቅድም ብለዋል።

    አሜሪካ ጠንካራ አቋም ትወስዳለች ሲሉም አክለዋል።

    ፕሬዚዳንቱ አክለውም ኢራንን በሚመለከት “በቀኑ መጨረሻ ላይ ተጨማሪ መረጃ” እንደሚሰጡ ተናግረዋል።

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም መዝጋቷን ካስታወቀች በኋላ የኢራን አብዮታዊ ዘብ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ተኩስ መክፈቱ ተሰምቷል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ መሳሪያ የታጠቁ ጀልባዎች ነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ተኩስ መክፈታቸውን የገለጸው የዩኬ የባሕር ትራንስፖረት ማዕከል ነው።

    አብዮታዊ ዘቡ በነዳጅ ጫኝ መርከቡ ላይ የተኮሰ ቢሆንም የመርከቢቷ ሠራተኞች በደህና ሁኔታ ላይ መሆናቸው ተገልጿል።

  7. ኢራን ጦርነቱ እስኪያበቃ ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመቆጣጠር “ቁርጠኛ’ መሆኑን የደህንነት ምክር ቤቱ አስታወቀ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የምታልፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የደህንነት ምክር ቤት ቴህራን በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን “ጦርነቱ እስኪያበቃ እና በቀጣናው ዘላቂ ሰላም እስኪሰፍን ድረስ ለመቆጣጠር እና ለመከታተል ቁርጠኛ ነች” አለ።

    የአገሪቱ ደህንነት በበላይነት የሚቆጣጠረው ምክር ቤቱ ክትትሉን እና ቁጥጥሩን የሚያደርገው በወሽመጡ የሚተላለፉ መርከቦችን መረጃ በመሰብሰብ እና የይለፍ ወረቀት በመስጠት እንዲሁም ለተገቢው አገልግሎት ክፍያን በመቀበል መሆኑን አስታውቋል።

    የደህንነት ምክር ቤቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በሰጠው መግለጫ "ጠላት የመርከቦችን መተላለፊያ ለማስተጓጎል እና የባህር ላይ እገዳን ተግባራዊ ማድረግ እስከቀጠለ ድረስ ኢራን ይህንን የተኩስ አቁም ጥሰት አድርጋ ትቆጥረዋለች” ብሏል።

    በተጨማሪም “የሆርሙዝ ወሽመጥን በሁኔታዎች እና ውሱን በሆነ መልኩ እንዳይከፈት ታደርጋለች" ሲል አክሏል።

    ጦርነቱን ለማቆም ስለሚደረገው ድርድር ምክር ቤቱ ቴህራን አሜሪካ ያቀረበችውን ምክረ ሃሳብ "እየገመገመች ሲሆን እስካሁን ምላሽ አልሰጠችም" ብሏል።

  8. የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ዛሬ በሊባኖስ አንድ ፈረንሳዊ ወታደር መገደሉን ተናገሩ

    ኢማኑኤል ማርኮን

    የፎቶው ባለመብት, PA Media

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑዔል ማርኮን በኤክስ ገጻቸው ላይ በሊባኖስ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ውስጥ አባል የሆነ ፈረንሳዊ ዛሬ ማለዳ በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል መገደሉን አስታወቁ።

    የመንግሥታቱ ድርጅት የሰላም ማስጠበቅ ተልዕኮ አባል የሆኑ ሌሎች ሦስት ወታደሮች መጎዳታቸውን እና ከአካባቢው እንዲወጡ መደረጉን ፕሬዚዳንቱ ጨምረው አስታውቀዋል።

    ማርኮን አሁን ባለው መረጃ ለጥቃቱ ተጠያቂው ሄዝቦላህ ነው ብለዋል።

    አክለውም የሊባኖስ ባለሥልጣናት ጥቃቱን ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩት ሰዎች በፍጥነት በቁጥጥር ሥር እንዲያውሉ ጠይቀዋል።

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም በፈረንሳይ የሰላም አስከባሪ ወታደሮች ላይ የደረሰውን ጥቃት አውግዘዋል።

    "የዚህን ጥቃት ሁኔታ ለማወቅ እና አጥፊዎችን ተጠያቂ ለማድረግ አፋጣኝ ምርመራ እንዲደረግ ጥብቅ መመሪያ አውጥቻለሁ" ሲሉ በኤክስ ፈገጻቸው ላይ በለጠፉት መልዕከት ላይ ተናግረዋል።

    “ይህ ኃላፊነት የጎደለው ድርጊት በሊባኖስ እና በሚደግፏት ወዳጅ የዓለም አገራት ጋር ባላት ግንኙነት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያደርስ ሳልገልጽ ማለፍ አልፈልግም።”

    ሳላም ጥቃቱን ማን እንደፈጸመው አልገለጹም።

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

  9. በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች በኢራን ጦር ተኩስ ተከፈተባቸው

    ጥቃቱ የደረሰበት አካባቢ

    የፎቶው ባለመብት, UKMTO

    አንድ መርከብ በሆርሙዝ ወሽመጥ ሲያልፍ በኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሚመሩ ሁለት መሣሪያ የታጠቁ ጀልባዎች ተኩስ እንደተከፈተበት የዩኬ የባሕር ላይ ትራንስፖርት ሥራዎች አስታወቀ።

    ክስተቱ የተፈጠረው በኦማን ሰሜን ምሥራቅ ግዛት 40 ኪሎ ሜትር ርቀት አካባቢ መሆኑ ታውቋል።

    መርከቡ እና ሠራተኞች ደኅና መሆናቸውን ዩኬ ማሪታይም ንግድ ሥራዎች ገልጿል።።

    ከዚህ ውጭ ቢያንስ ሁለት የንግድ መርከቦች ወሽመጡን ለመሻገር ሲሞክሩ የጥይት ሩምታ እንደተከፈተባቸው ሮይተርስ የዜና ወኪል ሦስት ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።

    ሮይተርስ መርከቦች ከኢራን ባሕር ኃይል ወሽመጡ መዘጋቱን የሚያሳውቅ የራዲዮ መልዕክት እንደደረሳቸውም ዘግቧል።

    የኢራን ባሕር ኃይል አንድም መርከብ በወሽመጡ እንዲያልፍ አልተፈቀደለትም ማለታቸውን ምንጮች ተናግረዋል።

  10. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት የወሰደችው እርምጃ ትራምፕ ጦርነቱ በቅርብ በስምምነት እንደሚፈታ መናገራቸውን አጠራጣሪ አደረገ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚንቀሳቀስ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ምን እየተፈጠረ እንደሆነ በእርጠኝነት መናገር ከባድ ሆኗል።

    በብሔራዊ መገናኛ ብዙኃኑ የተላለፈው የኢራን ወቅታዊ መልዕክት አሜሪካ በወደቦች ላይ የጣለችው እግድ ተፈፃሚነቱ በመቀጠሉ ምክንያት የሆርሙዝ ወሽመጥ በድጋሚ ተዘግቷል የሚል ነው።

    እንደ ቴህራን ከሆነ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች በሚገቡ እና በሚወጡ መርከቦች ላይ የጣለችው እግድ አሁንም ተፈፃሚ ነው ማለት ነው።

    ኢራናዊያን ከጥቂት ቀናት በፊት ወደ ነበርንበት እንመለሳለን እያሉ ሲሆን፤ ይህም ወሽመጡ በኢራን ጦር ቁጥጥር ስር ተመልሷል ማለት ነው።

    እስካሁን ከዋይት ሐውስ የተሰጠ ምላሽ አልተሰማም። በዋሽንግተን ዲሲ ሌሊቱ ተገባዶ አዲስ ቀን ሲጀመር መስማታችን ግን አይቀሬ ነው።

    ትናንት ፕሬዝዳንት ትራምፕ የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ ለሙሉ እንደተከፈተ እና ለንግድ መርከቦች መተላለፊያነት ዝግጁ መሆኑን ያበሰሩትን ዜና ማየት አልተቻለም።

    በተመሳሳይ ጊዜ የተከማቸውን የበለፀገ ዩራኒየም አሳልፎ መስጠትን ጨምሮ ኢራን ያቀረቧቸውን መደራደሪያዎች ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተቀብላ መስማማቷን ገልፀዋል። ይህን ስምምነት ግን ኢራን ሐሰት ነው ብላለች።

    ትራምፕ ከቴህራን ጋር ትልቅ ስምምነት መፈፀማቸው የማይቀር እንደሆነ ጠቁመዋል።

    በኢራን የተወሰደው እርምጃ ይህን ስምምነት እውን የሚያደርግ አይመስልም።

    አሁንም ድረስ በሁለቱም ወገኖች የሚወጡ የሚዲያ መልዕክቶች ከትዕይንቱ በስተጀርባ ጸጥ ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ያካተተ ስለመሆኑ ማወቅ ከባድ ነው።

    ባለፈው ሳምንት በፓኪስታን ያለ ውጤት የተጠናቀቀውን ንግግር ተከትሎ ሁለቱ ወገኖች ሁለተኛ ዙር ንግግር ያደርጋሉ የሚል የተወሰነ ተስፋ አለ።

  11. የሆርሙዝ ወሽመጥ ተዘግቷል የሚሉ ዘገባዎች ከወጡ በኋላ መርከቦች አቅጣጫ እየቀየሩ ነው

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የመርከቦች እንቅስቃሴ

    የፎቶው ባለመብት, MarineTraffic

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ከአንድ ሰዓት በፊት የቴህራን ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቱን ከዘገበ በኋላ በርካታ መርከቦች አቅጣጫቸውን እየቀየሩ መሆናቸው ታይቷል።

    ነዳጅ የጫነው እና የግሪክን ሰንደቅ ዓላማ የሚያውለበልበው ሚኒርቫ ኤቨሮፒ የተሰኘ አንድ መርከብ መጀመሪያ ወደተነሳበት አቅጣጫ ሲመለስ ታይቷል።

  12. የኢራን ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መዝጋቱን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ

    የኢራን ጦር ጀልባ

    የፎቶው ባለመብት, NurPhoto via Getty images

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱ ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም መቆጣጠር እንደጀመረ መግለጹን ዘገቡ።

    ፋርስ የዜና ወኪል፣ የኢራን የተማሪዎች ዜና ወኪል እንዲሁም ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃኑ ኢሪብ አብዮታዊ ዘቡን ጠቅሰው የወሽመጡ አካባቢን ጦሩ ተቆጣጥሮ “በቀደመ ሁኔታው ላይ” መመለሱን ዘግበዋል።

    የተወሰኑ የጭነት መርከቦች በወሽመጡ በኩል ማለፍ ችለው ነበር።

    አብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው አሜሪካን “በባሕር ላይ ውንብድና” ወንጅሎ “እገዳ የምትለው” ከባሕር ላይ ዘረፋ አይተናነስም ብሏል።

    ኢራን ቀደም ሲል ወደቦቿ ተዘግተው የሚቆዩ ከሆነ ወሽመጡን እንደምትዘጋ ዝታ ነበር።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን በስተደቡብ የሚገኝ ጠባብ መተላለፊያ ሲሆን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ይጓጓዝበታል።

    ኢረን ከአሜሪካ ያደረገችው ድርድር ያለ ስምምነት መጠናቀቁን ተከትሎ የአሜሪካ ጦር ወደ ኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይገቡ እና እንዳይወጡ ለማድረግ እገዳ ጥሏል።

    የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ግን እገዳው ካልተነሳ ሆርሙዝን እንደሚዘጉ ሲያስጠነቀቅቁ ቆይተዋል።

  13. ኢራን በከፊል የአየር ክልሏን ከፈተች- የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን

    የኢራን አየር ክልል እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ጥቃት መፈጸም ከጀመሩ አንስቶ ለማንኛውም በረራ ዝግ ሆኖ ቆይቷል።

    የፎቶው ባለመብት, Bloomberg via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን አየር ክልል እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ጥቃት መፈጸም ከጀመሩ አንስቶ ለማንኛውም በረራ ዝግ ሆኖ ቆይቷል

    ኢራን በከፊል የአየር ክልሏን ለዓለም አቀፍ በረራዎች ክፍት ማድረጓን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ኢርና ዘገበ።

    የአገሪቱ ሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣን የአገሪቱ የአየር ክልል እና ክፍት የሆኑ አውሮፕላን ማረፊያዎችን አስታውቋል።

    በአገሪቱ ሰዓት አቆጣጠር ከ7፡00 (ምሽት 12:30) ጀምሮ የአየር ክልሏ በከፊል ክፍት እንደሚሆን የተገለጸ ሲሆን ከዛሬ ጀምሮ ቀስ በቀስ በረራዎች ይጀምራሉ ሲል ኢርና ዘግቧል።

    በአገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል የሚገኙ የበረራ መስመሮች ለዓለም አቀፍ በረራዎች ክፍት መሆናቸውንም መገናኛ ብዙኃኑ አስታውቋል።

    የኢራን አየር ክልል እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ጥቃት መፈጸም ከጀመሩ አንስቶ ለማንኛውም በረራ ዝግ ሆኖ ቆይቷል።

  14. በኢራን እና ሊባኖስ የተደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነቶች የያዙት ተስፋ እና አደጋ

    በሊባኖስ የተደረሰውን የተኩስ አቁም ተከትሎ ወደ መኖሪያ ቀያቸው የሚመለሱ ሊባኖሳውያን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሐሙስ ምሽት በእስራኤል እና በኢራን በሚደገፈው ሄዝቦላህ መካከል የሚደረገው ጦርነት ለአስር ቀናት እንዲቆም መደረጉ ለኢራን ድል ነው።

    በቴህራን ያለው አገዛዝ በሊባኖስ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ ጠይቆ ነበር፤ ያለበለዚያ ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ውይይት ሊቀጥል፤ ሊሰምርም አይችልም ሲል ተደምጧል።

    ኢራን አሁን የተኩስ አቁሙን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ "ሙሉ በሙሉ ክፍት" መሆኑን በመግለጽ ምላሽ ሰጥታለች።

    ባለፈው ቅዳሜና እሁድ በኢዝላማባድ የተደረገው ረዥም ድርድር እንደሚያሳየው፣ በሊባኖስ የነበረው ጦርነት እየቀጠለ ቢሆንም ከመግባባት ላይ ለመድረስ ዕድል መኖሩን አመላክቷል።

    ነገር ግን ኢራን እና ፓኪስታን በተኩስ አቁም ላይ ሊባኖስ መካተት እንዳለባት አጥብቀው ተሟግተዋል።

    በእስራኤል ላሉ አንዳንዶች አሁንም ኢራን ጨዋታው ሜዳ ላይ የበላይ ሆና ወጥታለች። ዛሬም የእስራኤል የረዥም ጊዜ ጠላት ሁኔታዎችን የምትዘውር እና የቀጣናውን ፖለቲካ የምትወስን ሆናለች።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ለአሜሪካው ወዳጃቸው ፍላጎቶች እጃቸውን ሰተዋል ብለው የተቆጡም አልጠፉም።

    በእነዚህ አንዳቸው ከሌላኛቸው ጋር በተጋመዱ ግጭቶች ውስጥ የተሳተፉ ሁሉም ተፋላሚዎች ከቅርብ ጊዜው ስምምነት የየድርሻቸውን ማግኘታቸውን አይቀርም።

    ለአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና በኢራን ላለው አመራር፣ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ በማድረጋቸው ዕውቅና ይቸራቸዋል።

    ኔታንያሁ በበኩላቸው የእስራኤል ወታደሮች በደቡባዊ ሊባኖስ እንደሚቆዩ ሊያስረዱ ይችላሉ።

    ለሊባኖስ መንግሥት ደግሞ ከወራት ሙከራ እና ጥረት በኋላ ከእስራኤል ጋር ቀጥተኛ ድርድር የማድረግ ዕድል አግኝቷል።

    ሄዝቦላህ ደግሞ ምንም እንኳ አሁንም "ጣቴ በቃታው ላይ" ቢሆንም የተኩስ አቁሙን አከብራለሁ ብሏል።

    ነገር ግን ትጥቅ እንደማይፈታ አጥብቆ ይናገራል።

  15. መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ እያለፉ መሆኑን የመርከቦች መረጃ አመለከተ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚተላለፉ መርከቦችን የሚያሳይ መረጃ

    የፎቶው ባለመብት, MarineTraffic

    የምስሉ መግለጫ, መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ እያለፉ ነው

    መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ ውስጥ እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ማሪን ትራፊክ የተሰኘ ገፅ መረጃ ያሳያል።

    እንደ ድረ ገፁ ገለጻ በርካታ ነዳጅ፣ ፈሳሽ ጋዝ እና ኬሚካሎችን የጫኑ መርከቦች በወሽመጡ ሲንቀሳቀሱ የሚታዩ ሲሆን፤ መርከቦቹ ወደ ዋናው የባሕር ኮሪደር ሲያቋርጡ ይታያሉ።

  16. ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ማን ምን አለ?

    በኦማን የባሕር ዳርቻ ላእ ኣለች መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ትራምፕ - የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በመካከለኛው ምሥራቅ ከኢራን ጋር “በጥሩ ሁኔታ እየሄደ ያለ ይመስላል” ሲሉ ተናግረዋል። በሳምንቱ መጨረሻ ድርድር እንደሚካሄድ እና አሁን መናገር የማይችሉት “አንድ ጥሩ ዜና” መኖሩንም ተናግረዋል። ትራምፕ በትናንትናው እለት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ የአሜሪካ የባሕር ኃይል "ከኢራን ጋር ያለው ስምምነት መቶ ፐርሰንት እስኪጠናቀቅ" ድረስ ወደቦቿን ዘግቶ ይቆያል ብለዋል።

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ - ሞሃመድ ባገር ጋሊባፍ ዩናይትድ ስቴትስ ከኢራን ጋር ባደረገችው ጦርነት ማሸነፏን አስመልክቶ ዶናልድ ትራምፕ የሰጡት አስተያየት “ሐሰት” ነው ብለዋል። አክለውም አሜሪካ እገዳውን ከቀጠለች የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ " ክፍት ሆኖ አይቆይም "ብለዋል።

    የአውሮፓ መሪዎች - የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ማክሮን እና የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር ትናንት በፓሪስ ወደ 40 ከሚጠጉ አገራት ባካሄዱት ስብሰባ የባህር ወሽመጡን በመክፈት ላይ ተነጋግረዋል። ስታርመር እንዳሉት ዩናይትድ ኪንግደም እና ፈረንሣይ በባሕሩ ላይ የሚደረግ የመርከብ ትራንስፖርት ነፃነትን ለመጠበቅ “ሁኔታዎች ሲፈቅዱ ሰላማዊ እና መከላከል ላይ ብቻ ያተኮረ” ዓለም አቀፍ ተልእኮ እንደሚመሩ ተናግረዋል።

    የቻይናው ፕሬዝዳንት - ትራምፕ የቻይናው ፕሬዝዳንት ዢ ጂንፒንግ "የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ በመከፈቱ እና/ወይም በፍጥነት በመከፈቱ በጣም ደስተኛ ናቸው" ብለዋል። የዩኤስ ፕሬዝዳንት በቻይና ከግንቦት 14-15 በቻይና በሚያደርጉት ጉብኝት ወቅት ከዢ ጂንፒንግ ጋር የሚያደርጉት ውይይት “ልዩ እና ምናልባትም ታሪካዊ ይሆናል” ብለዋል።

  17. የእስራኤል ጦር በኢራን ላይ ወደ 11,000 የሚጠጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታወቀ

    በእስራኤል ትቃት የወደሙ አካባቢዎች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት በኢራን ላይ ከፈጸመው የቦምብ ድብደባ ጋር የተያያዙ አዳዲስ አሃዞችን ይፋ አድርጓል።

    በዚህም ለስድስት ሳምንት በተካሄደው ጦርነት ወቅት በአገሪቱ ላይ ወደ 10,800 የሚጠጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታውቋል።

    መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች የዜና ኤጀንሲ (ሂራና) የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ለሁለት ሳምንታት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት መደረሱን እስካወጁበት ሚያዝያ 7 ድረስ 1,701 ሰላማዊ ኢራናውያን መገደላቸውን ዘግቧል።

    የመከላከያ ሠራዊቱ በሊባኖስ ከ14,900 በላይ የመድፍ ድብደባዎችን እና 2,500 የአየር ድብደባዎችን መፈጸሙን ይፋ አደርጓል።

    አክሎም በግምት 165 ባለ ብዙ ሕንጻዎችን መምታቱን አስታውቋል።

    የሊባኖስ የጤና ባለሥልጣናት በሊባኖስ ለስድስት ሳምንታት በዘለቀው የአየር ጥቃት 2,100 ሰዎች መሞታቸውን እና ከአንድ ሚሊዮን በላይ መፈናቀላቸውን ተናግረዋል።

  18. ትራምፕ፣ የቻይናው መሪ ስለ ሆርሙዝ “በጣም ደስተኛ” መሆናቸውን ተናገሩ

    ትራምፕ እና ዢ በደቡብ ኮሪያ በተገናኙበት ወቅት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዶናልድ ትራምፕ የቻይናው ፕሬዝዳንት ዢ ጂንፒንግ "የሆርሙዝ ወሽመጥ ክፍት እና/ወይም በፍጥነት በመከፈቱ በጣም ደስተኛ ናቸው" ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ትራምፕ በቻይና ግንቦት 14 እና 15 የሚያደርጉት ስብሰባ እንደሚካሄድ እና "ልዩ እና ምናልባትም ታሪካዊ" እንደሚሆን ተናግረዋል።

    "ብዙ ነገር ይሳካል!"

    ቻይና ትልቋ የኢራን ነዳጅ ገዢ ስትሆን 38 በመቶ የሚሆነውን ነዳጇን የምታገኘው በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ በኩል ነው።

    ቻይና፣ ኢራን ከአሜሪካ ጋር እንድትደራደር በማሳሰብ ረገድ ወሳኝ ሚና ተጫውታለች። እንዲሁም የተኩስ አቁም ስምምነቱን እና የሰላም ድርድሩን እንደገና መጀመርን እንደምትደግፍ ትናገራለች።

  19. የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ የአሜሪካ እገዳ የሚቀጥል ከሆነ ሆርሙዝ “ክፍት ሆኖ አይቆይም” ሲሉ አስጠነቀቁ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋሊባፍ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋሊባፍ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ ዶናልድ ትራምፕ “በአንድ ሰዓት ውስጥ ሰባት ነገሮችን ተናግረዋል፤ ሰባቱም ሐሰት ናቸው” ብለዋል።

    ጋሊባፍ “ጦርነቱን አላሸነፉም፤ በዚህ ውሸታቸው በድርድሮቹ የትም መድረስ እንደማይችሉ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል” ብለዋል።

    አፈ ጉባዔው ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ሲናገሩም “የአሜሪካ እገዳ ስለቀጠለ”፤ “እንደተዘጋ ይቆያል” ብለዋል።

    የአፈጉባዔው አስተያየት ከዚህ ቀደም በኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የተባለውን ያረጋገጠ ሆኗል።

    “ወሽመጡ ክፍትም ሆነ ዝግ የሚመራበት ደንብ የሚወሰነው መሬት ላይ እንጂ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ አይደለም” ብለው ነበር።

    ጋሊባፍ አስተያየታቸውን የሰጡት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በኤክስ ገጻቸው ላይ በእንግሊዘኛ የሆርሙዝ ወሽመጥ “በቀረው የተኩስ አቁሙ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ክፍት ነው” ካሉ በኋላ “ለሁሉም የንግድ መርከቦች ማለፍ ተፈቅዷል” ብለው ነበር።

    የአራጋቺ አስተያየት የተለያዩ ትችቶችን አስተናግዷል። የኢራን መገናኛ ብዙኃን እና ወግ አትባቂዎች ምን ማለታቸው እንደሆነ "ግልጽ" እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።

    ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ "የመገናኛ ብዙኃን ፐሮፖጋንዳ እና የሕዝብ አስተያየትን መቅረጽ የጦርነት አስፈላጊ አካል ናቸው፤ የኢራን ሕዝብ ግን በእነዚህ ስልቶች ተጽዕኖ አይደረግበትም" ብለዋል።

  20. በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ ጉዞ የኢራን አብዮታዊ ዘብ ፈቃድ እንደሚያስፈልገው ተዘገበ

    በሆርሙዝ የሚያልፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በሆርሙዝ በኩል የሚያልፉ “ሁሉም የንግድ መርከቦች ሚያደርጉት ጉዞ ለቀሪው የተኩስ አቁሙ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ክፍት እንዲሆን መታወጁን” በኤክስ ገጻቸው አስታውቀው ነበር።

    የኢራን መንግሥት የቴሌቪዥን ጣቢያ አንድ “ከፍተኛ ወታደራዊ ባለሥልጣንን” ጠቅሶ ባስተላለፈው ዘገባ፤ የመርከቦቹ ጉዞ የሚከናወነው “በተለየ መስመር” እንደሆነ ገልጿል። መርከቦቹ ለማለፍ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል ፈቃድ እንደሚያስፈልጋቸውም ጠቅሷል።

    ባለሥልጣኑ ለቴሌቪዥን ጣቢያው እንደተናገሩት፤ ይህ የተለየ የጉዞ መስመር የተወሰነው በኢራን የወደቦች እና ማሪታይም ድርጅት ነው።

    ጣቢያው ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣኑን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚደረግ የወታደራዊ መርከቦች ጉዞ አሁንም ቢሆን "የተከለከለ" ነው።

    በሌላ በኩል የመርከብ ጉዞ ኩባንያዎች የሆርሙዝ ደኅንነት እስከሚረጋገጥ ድረስ ወሽመጡን እንደማይጠቀሙ ተናግረዋል። ቢቢሲ ያነጋገረው አንድ የነዳጅ እና የጋዝ ጫኝ መርከቦች ኦፕሬተር፤ ለጊዜው የኢራን መግለጫ “ምንም የሚቀይረው ነገር የለም” ብሏል።

    “አላስፈላጊ አደጋ ውስጥ መግባት አለብን ብለን አናስብም፤ የኩባንያችን በወሽመጡ በኩል ቀድሞ የሚያልፍ ተቋም እንሆናለን የሚል አቋም የለውም” ሲል ገልጿል።

    በቀጣናው የሚገኙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ኦፕሬተር የሆነው ‘ስቴና በልክ’ የተሰኘው ኩባንያ በበኩሉ “ሁኔታውን በቅርበት እየተከታተለ” መሆኑን አስታውቋል።

    “የእያንዳንዱ ጉዟችን ውሳኔ የሚመሠረተው የሠራተኞቻችን እና የመርከቦቻችን ደኅንነት ላይ ነው፤ ደኅንነቱ የተጠበቀ መሆኑን እስካላረካን ድረስ ጉዞ አንጀምርም” ብሏል።