በኢራን ድርድር የመጨረሻው ውሳኔ የማን ነው?

የፎቶው ባለመብት, WANA/Reuters
የኢራን ፕሬዝዳንት መሱድ ፔዘሽኪያን “የትኛውም ውሳኔ” ያለ የኢራን ሦስተኛ ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሚኔ “ፍቃድ” አይወሰንም ብለዋል።
ፕሬዝዳንቱ ይህን ያሉት ወግ አጥባቂ አመለካከት ያላቸው ኢራናዊ የፓርላማ አባል ካምራን ጋዛንፋሪ በሳምንቱ መጀመሪያ የተኩስ አቁም ስምምነቱን “ያለ ኻሚኔ ፍቃድ” ተቀብለዋል በማለት ከተቹ በኋላ ነው።
የ56 ዓመቱ የኢራን አዲሱ ጠቅላይ መሪ ከተሾሙ ወዲህ በሕዝብ ፊት ታይተው አያውቁም። በአንፃሩ እንደ ኢራን መገናኛ ብዙኃን ገለፃ ጠቅላይ መሪው በርካታ የጽሑፍ መግለጫዎችን አስተላልፈዋል።
ነገር ግን ፔዘሽኪያንን ጨምሮ በርካታ ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣናት በቅርብ ሳምንታት ከኻሚኔ ጋር ተገናኝተዋል ተብሏል።
ኻሚኔ በጽሑፍ መልዕክቶቻቸው አሜሪካን እና እስራኤልን በመቃወም የኢራንን አቋም ያረጋገጡ ሲሆን፤ ስለ አሁኑ ድርድር ግን አስተያየት አልሰጡም።
የጠቅላይ መሪው የጤና ሁኔታ ጥርጣሬ ላይ የወደቀም ሲሆን፤ አባታቸው አሊ ኻሚኔ ሲገደሉ እርሳቸውም ቆስለዋል ተብሎ ይገመታል።
የአሜሪካ መከላከያ ኃላፊ ፒት ሄግሴት ቀደም ሲል ኻሚኔ “በከፍተኛ ደረጃ ተጎድተው ሊሆን ይችላል” ብለው ነበር። ይህን ግን የኢራን ጤና ሚኒስቴር አስተባብሏል።



















