ኢራን ሆርሙዝን ዳግም ስትዘጋ ነዳጅ እና ኮንቴይነር የጫኑ መርከቦች ጥቃት እንደተፈጸመባቸው ገለጹ

የአሜሪካ ባሕር ኃይል ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች ላይ የጣለው እገዳን በመቀጠሉ፣ ቴህራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷን አስታውቃለች። ይህንንም ተከትሎ ነዳጅ እና ኮንቴይነር የጫኑ መርከቦች ጥቃት እንደተፈጸመባቸው አስታውቀዋል። የዩኬ የባሕር ትራንስፖርት አገልግሎት ጥቃቱ የተፈጸመው በኦማን የባሕር ዳርቻ መሆኑን ገልጿል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ ኢራን “ልታስፈራራን አትችልም” አሉ

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ የኢራን ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግመኛ መዝጋቱን ካስታወቀ በኋላ በሰጡት ምላሽ ቴህራን “ልታስፈራራን አትችልም” አሉ።

    “ለረዥም ዓመታት እንዳደረጉት የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመዝጋት ይፈልጋሉ” ሲሉ ለጋዜጠኞች የተናገሩት ትራምፕ “ሊያስፈራሩን አይችሉም” ብለዋል።

    ትራምፕ ከኢራን ጋር “በጣም ጥሩ ውይይት እየተካሄደ ነው” በማለት ቴህራን “ላለፉት 47 ዓመታት እንደነበሩት ለማታለል እየሞከሩ ነው” ብለዋል።

    የኢራን ባለሥልጣናት የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመዝጋት ይፈልጋሉ ያሉት ትራምፕ፣ አሜሪካን “እንድታስፈራራ” አንፈቅድም ብለዋል።

    አሜሪካ ጠንካራ አቋም ትወስዳለች ሲሉም አክለዋል።

    ፕሬዚዳንቱ አክለውም ኢራንን በሚመለከት “በቀኑ መጨረሻ ላይ ተጨማሪ መረጃ” እንደሚሰጡ ተናግረዋል።

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም መዝጋቷን ካስታወቀች በኋላ የኢራን አብዮታዊ ዘብ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ተኩስ መክፈቱ ተሰምቷል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ መሳሪያ የታጠቁ ጀልባዎች ነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ተኩስ መክፈታቸውን የገለጸው የዩኬ የባሕር ትራንስፖረት ማዕከል ነው።

    አብዮታዊ ዘቡ በነዳጅ ጫኝ መርከቡ ላይ የተኮሰ ቢሆንም የመርከቢቷ ሠራተኞች በደህና ሁኔታ ላይ መሆናቸው ተገልጿል።

  2. ኢራን ጦርነቱ እስኪያበቃ ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥን ለመቆጣጠር “ቁርጠኛ’ መሆኑን የደህንነት ምክር ቤቱ አስታወቀ

    የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የደህንነት ምክር ቤት ቴህራን በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን “ጦርነቱ እስኪያበቃ እና በቀጣናው ዘላቂ ሰላም እስኪሰፍን ድረስ ለመቆጣጠር እና ለመከታተል ቁርጠኛ ነች” አለ።

    የአገሪቱ ደህንነት በበላይነት የሚቆጣጠረው ምክር ቤቱ ክትትሉን እና ቁጥጥሩን የሚያደርገው በወሽመጡ የሚተላለፉ መርከቦችን መረጃ በመሰብሰብ እና የይለፍ ወረቀት በመስጠት እንዲሁም ለተገቢው አገልግሎት ክፍያን በመቀበል መሆኑን አስታውቋል።

    የደህንነት ምክር ቤቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በሰጠው መግለጫ "ጠላት የመርከቦችን መተላለፊያ ለማስተጓጎል እና የባህር ላይ እገዳን ተግባራዊ ማድረግ እስከቀጠለ ድረስ ኢራን ይህንን የተኩስ አቁም ጥሰት አድርጋ ትቆጥረዋለች” ብሏል።

    በተጨማሪም “የሆርሙዝ ወሽመጥን በሁኔታዎች እና ውሱን በሆነ መልኩ እንዳይከፈት ታደርጋለች" ሲል አክሏል።

    ጦርነቱን ለማቆም ስለሚደረገው ድርድር ምክር ቤቱ ቴህራን አሜሪካ ያቀረበችውን ምክረ ሃሳብ "እየገመገመች ሲሆን እስካሁን ምላሽ አልሰጠችም" ብሏል።

  3. የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ዛሬ በሊባኖስ አንድ ፈረንሳዊ ወታደር መገደሉን ተናገሩ

    የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑዔል ማርኮን በኤክስ ገጻቸው ላይ በሊባኖስ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ውስጥ አባል የሆነ ፈረንሳዊ ዛሬ ማለዳ በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል መገደሉን አስታወቁ።

    የመንግሥታቱ ድርጅት የሰላም ማስጠበቅ ተልዕኮ አባል የሆኑ ሌሎች ሦስት ወታደሮች መጎዳታቸውን እና ከአካባቢው እንዲወጡ መደረጉን ፕሬዚዳንቱ ጨምረው አስታውቀዋል።

    ማርኮን አሁን ባለው መረጃ ለጥቃቱ ተጠያቂው ሄዝቦላህ ነው ብለዋል።

    አክለውም የሊባኖስ ባለሥልጣናት ጥቃቱን ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩት ሰዎች በፍጥነት በቁጥጥር ሥር እንዲያውሉ ጠይቀዋል።

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም በፈረንሳይ የሰላም አስከባሪ ወታደሮች ላይ የደረሰውን ጥቃት አውግዘዋል።

    "የዚህን ጥቃት ሁኔታ ለማወቅ እና አጥፊዎችን ተጠያቂ ለማድረግ አፋጣኝ ምርመራ እንዲደረግ ጥብቅ መመሪያ አውጥቻለሁ" ሲሉ በኤክስ ፈገጻቸው ላይ በለጠፉት መልዕከት ላይ ተናግረዋል።

    “ይህ ኃላፊነት የጎደለው ድርጊት በሊባኖስ እና በሚደግፏት ወዳጅ የዓለም አገራት ጋር ባላት ግንኙነት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያደርስ ሳልገልጽ ማለፍ አልፈልግም።”

    ሳላም ጥቃቱን ማን እንደፈጸመው አልገለጹም።

  4. በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች በኢራን ጦር ተኩስ ተከፈተባቸው

    አንድ መርከብ በሆርሙዝ ወሽመጥ ሲያልፍ በኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሚመሩ ሁለት መሣሪያ የታጠቁ ጀልባዎች ተኩስ እንደተከፈተበት የዩኬ የባሕር ላይ ትራንስፖርት ሥራዎች አስታወቀ።

    ክስተቱ የተፈጠረው በኦማን ሰሜን ምሥራቅ ግዛት 40 ኪሎ ሜትር ርቀት አካባቢ መሆኑ ታውቋል።

    መርከቡ እና ሠራተኞች ደኅና መሆናቸውን ዩኬ ማሪታይም ንግድ ሥራዎች ገልጿል።።

    ከዚህ ውጭ ቢያንስ ሁለት የንግድ መርከቦች ወሽመጡን ለመሻገር ሲሞክሩ የጥይት ሩምታ እንደተከፈተባቸው ሮይተርስ የዜና ወኪል ሦስት ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።

    ሮይተርስ መርከቦች ከኢራን ባሕር ኃይል ወሽመጡ መዘጋቱን የሚያሳውቅ የራዲዮ መልዕክት እንደደረሳቸውም ዘግቧል።

    የኢራን ባሕር ኃይል አንድም መርከብ በወሽመጡ እንዲያልፍ አልተፈቀደለትም ማለታቸውን ምንጮች ተናግረዋል።

  5. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት የወሰደችው እርምጃ ትራምፕ ጦርነቱ በቅርብ በስምምነት እንደሚፈታ መናገራቸውን አጠራጣሪ አደረገ

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ምን እየተፈጠረ እንደሆነ በእርጠኝነት መናገር ከባድ ሆኗል።

    በብሔራዊ መገናኛ ብዙኃኑ የተላለፈው የኢራን ወቅታዊ መልዕክት አሜሪካ በወደቦች ላይ የጣለችው እግድ ተፈፃሚነቱ በመቀጠሉ ምክንያት የሆርሙዝ ወሽመጥ በድጋሚ ተዘግቷል የሚል ነው።

    እንደ ቴህራን ከሆነ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች በሚገቡ እና በሚወጡ መርከቦች ላይ የጣለችው እግድ አሁንም ተፈፃሚ ነው ማለት ነው።

    ኢራናዊያን ከጥቂት ቀናት በፊት ወደ ነበርንበት እንመለሳለን እያሉ ሲሆን፤ ይህም ወሽመጡ በኢራን ጦር ቁጥጥር ስር ተመልሷል ማለት ነው።

    እስካሁን ከዋይት ሐውስ የተሰጠ ምላሽ አልተሰማም። በዋሽንግተን ዲሲ ሌሊቱ ተገባዶ አዲስ ቀን ሲጀመር መስማታችን ግን አይቀሬ ነው።

    ትናንት ፕሬዝዳንት ትራምፕ የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ ለሙሉ እንደተከፈተ እና ለንግድ መርከቦች መተላለፊያነት ዝግጁ መሆኑን ያበሰሩትን ዜና ማየት አልተቻለም።

    በተመሳሳይ ጊዜ የተከማቸውን የበለፀገ ዩራኒየም አሳልፎ መስጠትን ጨምሮ ኢራን ያቀረቧቸውን መደራደሪያዎች ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተቀብላ መስማማቷን ገልፀዋል። ይህን ስምምነት ግን ኢራን ሐሰት ነው ብላለች።

    ትራምፕ ከቴህራን ጋር ትልቅ ስምምነት መፈፀማቸው የማይቀር እንደሆነ ጠቁመዋል።

    በኢራን የተወሰደው እርምጃ ይህን ስምምነት እውን የሚያደርግ አይመስልም።

    አሁንም ድረስ በሁለቱም ወገኖች የሚወጡ የሚዲያ መልዕክቶች ከትዕይንቱ በስተጀርባ ጸጥ ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ያካተተ ስለመሆኑ ማወቅ ከባድ ነው።

    ባለፈው ሳምንት በፓኪስታን ያለ ውጤት የተጠናቀቀውን ንግግር ተከትሎ ሁለቱ ወገኖች ሁለተኛ ዙር ንግግር ያደርጋሉ የሚል የተወሰነ ተስፋ አለ።

  6. የሆርሙዝ ወሽመጥ ተዘግቷል የሚሉ ዘገባዎች ከወጡ በኋላ መርከቦች አቅጣጫ እየቀየሩ ነው

    የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ከአንድ ሰዓት በፊት የቴህራን ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቱን ከዘገበ በኋላ በርካታ መርከቦች አቅጣጫቸውን እየቀየሩ መሆናቸው ታይቷል።

    ነዳጅ የጫነው እና የግሪክን ሰንደቅ ዓላማ የሚያውለበልበው ሚኒርቫ ኤቨሮፒ የተሰኘ አንድ መርከብ መጀመሪያ ወደተነሳበት አቅጣጫ ሲመለስ ታይቷል።

  7. የኢራን ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መዝጋቱን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱ ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም መቆጣጠር እንደጀመረ መግለጹን ዘገቡ።

    ፋርስ የዜና ወኪል፣ የኢራን የተማሪዎች ዜና ወኪል እንዲሁም ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃኑ ኢሪብ አብዮታዊ ዘቡን ጠቅሰው የወሽመጡ አካባቢን ጦሩ ተቆጣጥሮ “በቀደመ ሁኔታው ላይ” መመለሱን ዘግበዋል።

    የተወሰኑ የጭነት መርከቦች በወሽመጡ በኩል ማለፍ ችለው ነበር።

    አብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው አሜሪካን “በባሕር ላይ ውንብድና” ወንጅሎ “እገዳ የምትለው” ከባሕር ላይ ዘረፋ አይተናነስም ብሏል።

    ኢራን ቀደም ሲል ወደቦቿ ተዘግተው የሚቆዩ ከሆነ ወሽመጡን እንደምትዘጋ ዝታ ነበር።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን በስተደቡብ የሚገኝ ጠባብ መተላለፊያ ሲሆን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ይጓጓዝበታል።

    ኢረን ከአሜሪካ ያደረገችው ድርድር ያለ ስምምነት መጠናቀቁን ተከትሎ የአሜሪካ ጦር ወደ ኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይገቡ እና እንዳይወጡ ለማድረግ እገዳ ጥሏል።

    የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ግን እገዳው ካልተነሳ ሆርሙዝን እንደሚዘጉ ሲያስጠነቀቅቁ ቆይተዋል።

  8. ኢራን በከፊል የአየር ክልሏን ከፈተች- የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን

    ኢራን በከፊል የአየር ክልሏን ለዓለም አቀፍ በረራዎች ክፍት ማድረጓን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ኢርና ዘገበ።

    የአገሪቱ ሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣን የአገሪቱ የአየር ክልል እና ክፍት የሆኑ አውሮፕላን ማረፊያዎችን አስታውቋል።

    በአገሪቱ ሰዓት አቆጣጠር ከ7፡00 (ምሽት 12:30) ጀምሮ የአየር ክልሏ በከፊል ክፍት እንደሚሆን የተገለጸ ሲሆን ከዛሬ ጀምሮ ቀስ በቀስ በረራዎች ይጀምራሉ ሲል ኢርና ዘግቧል።

    በአገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል የሚገኙ የበረራ መስመሮች ለዓለም አቀፍ በረራዎች ክፍት መሆናቸውንም መገናኛ ብዙኃኑ አስታውቋል።

    የኢራን አየር ክልል እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ጥቃት መፈጸም ከጀመሩ አንስቶ ለማንኛውም በረራ ዝግ ሆኖ ቆይቷል።

  9. በኢራን እና ሊባኖስ የተደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነቶች የያዙት ተስፋ እና አደጋ

    ሐሙስ ምሽት በእስራኤል እና በኢራን በሚደገፈው ሄዝቦላህ መካከል የሚደረገው ጦርነት ለአስር ቀናት እንዲቆም መደረጉ ለኢራን ድል ነው።

    በቴህራን ያለው አገዛዝ በሊባኖስ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ ጠይቆ ነበር፤ ያለበለዚያ ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ውይይት ሊቀጥል፤ ሊሰምርም አይችልም ሲል ተደምጧል።

    ኢራን አሁን የተኩስ አቁሙን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ "ሙሉ በሙሉ ክፍት" መሆኑን በመግለጽ ምላሽ ሰጥታለች።

    ባለፈው ቅዳሜና እሁድ በኢዝላማባድ የተደረገው ረዥም ድርድር እንደሚያሳየው፣ በሊባኖስ የነበረው ጦርነት እየቀጠለ ቢሆንም ከመግባባት ላይ ለመድረስ ዕድል መኖሩን አመላክቷል።

    ነገር ግን ኢራን እና ፓኪስታን በተኩስ አቁም ላይ ሊባኖስ መካተት እንዳለባት አጥብቀው ተሟግተዋል።

    በእስራኤል ላሉ አንዳንዶች አሁንም ኢራን ጨዋታው ሜዳ ላይ የበላይ ሆና ወጥታለች። ዛሬም የእስራኤል የረዥም ጊዜ ጠላት ሁኔታዎችን የምትዘውር እና የቀጣናውን ፖለቲካ የምትወስን ሆናለች።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ለአሜሪካው ወዳጃቸው ፍላጎቶች እጃቸውን ሰተዋል ብለው የተቆጡም አልጠፉም።

    በእነዚህ አንዳቸው ከሌላኛቸው ጋር በተጋመዱ ግጭቶች ውስጥ የተሳተፉ ሁሉም ተፋላሚዎች ከቅርብ ጊዜው ስምምነት የየድርሻቸውን ማግኘታቸውን አይቀርም።

    ለአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና በኢራን ላለው አመራር፣ የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረስ በማድረጋቸው ዕውቅና ይቸራቸዋል።

    ኔታንያሁ በበኩላቸው የእስራኤል ወታደሮች በደቡባዊ ሊባኖስ እንደሚቆዩ ሊያስረዱ ይችላሉ።

    ለሊባኖስ መንግሥት ደግሞ ከወራት ሙከራ እና ጥረት በኋላ ከእስራኤል ጋር ቀጥተኛ ድርድር የማድረግ ዕድል አግኝቷል።

    ሄዝቦላህ ደግሞ ምንም እንኳ አሁንም "ጣቴ በቃታው ላይ" ቢሆንም የተኩስ አቁሙን አከብራለሁ ብሏል።

    ነገር ግን ትጥቅ እንደማይፈታ አጥብቆ ይናገራል።

  10. መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ እያለፉ መሆኑን የመርከቦች መረጃ አመለከተ

    መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ ውስጥ እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ማሪን ትራፊክ የተሰኘ ገፅ መረጃ ያሳያል።

    እንደ ድረ ገፁ ገለጻ በርካታ ነዳጅ፣ ፈሳሽ ጋዝ እና ኬሚካሎችን የጫኑ መርከቦች በወሽመጡ ሲንቀሳቀሱ የሚታዩ ሲሆን፤ መርከቦቹ ወደ ዋናው የባሕር ኮሪደር ሲያቋርጡ ይታያሉ።

  11. ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ማን ምን አለ?

    ትራምፕ - የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በመካከለኛው ምሥራቅ ከኢራን ጋር “በጥሩ ሁኔታ እየሄደ ያለ ይመስላል” ሲሉ ተናግረዋል። በሳምንቱ መጨረሻ ድርድር እንደሚካሄድ እና አሁን መናገር የማይችሉት “አንድ ጥሩ ዜና” መኖሩንም ተናግረዋል። ትራምፕ በትናንትናው እለት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ የአሜሪካ የባሕር ኃይል "ከኢራን ጋር ያለው ስምምነት መቶ ፐርሰንት እስኪጠናቀቅ" ድረስ ወደቦቿን ዘግቶ ይቆያል ብለዋል።

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ - ሞሃመድ ባገር ጋሊባፍ ዩናይትድ ስቴትስ ከኢራን ጋር ባደረገችው ጦርነት ማሸነፏን አስመልክቶ ዶናልድ ትራምፕ የሰጡት አስተያየት “ሐሰት” ነው ብለዋል። አክለውም አሜሪካ እገዳውን ከቀጠለች የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ " ክፍት ሆኖ አይቆይም "ብለዋል።

    የአውሮፓ መሪዎች - የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ማክሮን እና የዩኬ ጠቅላይ ሚኒስትር ስታርመር ትናንት በፓሪስ ወደ 40 ከሚጠጉ አገራት ባካሄዱት ስብሰባ የባህር ወሽመጡን በመክፈት ላይ ተነጋግረዋል። ስታርመር እንዳሉት ዩናይትድ ኪንግደም እና ፈረንሣይ በባሕሩ ላይ የሚደረግ የመርከብ ትራንስፖርት ነፃነትን ለመጠበቅ “ሁኔታዎች ሲፈቅዱ ሰላማዊ እና መከላከል ላይ ብቻ ያተኮረ” ዓለም አቀፍ ተልእኮ እንደሚመሩ ተናግረዋል።

    የቻይናው ፕሬዝዳንት - ትራምፕ የቻይናው ፕሬዝዳንት ዢ ጂንፒንግ "የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ በመከፈቱ እና/ወይም በፍጥነት በመከፈቱ በጣም ደስተኛ ናቸው" ብለዋል። የዩኤስ ፕሬዝዳንት በቻይና ከግንቦት 14-15 በቻይና በሚያደርጉት ጉብኝት ወቅት ከዢ ጂንፒንግ ጋር የሚያደርጉት ውይይት “ልዩ እና ምናልባትም ታሪካዊ ይሆናል” ብለዋል።

  12. የእስራኤል ጦር በኢራን ላይ ወደ 11,000 የሚጠጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታወቀ

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት በኢራን ላይ ከፈጸመው የቦምብ ድብደባ ጋር የተያያዙ አዳዲስ አሃዞችን ይፋ አድርጓል።

    በዚህም ለስድስት ሳምንት በተካሄደው ጦርነት ወቅት በአገሪቱ ላይ ወደ 10,800 የሚጠጉ ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታውቋል።

    መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች የዜና ኤጀንሲ (ሂራና) የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ለሁለት ሳምንታት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት መደረሱን እስካወጁበት ሚያዝያ 7 ድረስ 1,701 ሰላማዊ ኢራናውያን መገደላቸውን ዘግቧል።

    የመከላከያ ሠራዊቱ በሊባኖስ ከ14,900 በላይ የመድፍ ድብደባዎችን እና 2,500 የአየር ድብደባዎችን መፈጸሙን ይፋ አደርጓል።

    አክሎም በግምት 165 ባለ ብዙ ሕንጻዎችን መምታቱን አስታውቋል።

    የሊባኖስ የጤና ባለሥልጣናት በሊባኖስ ለስድስት ሳምንታት በዘለቀው የአየር ጥቃት 2,100 ሰዎች መሞታቸውን እና ከአንድ ሚሊዮን በላይ መፈናቀላቸውን ተናግረዋል።

  13. ትራምፕ፣ የቻይናው መሪ ስለ ሆርሙዝ “በጣም ደስተኛ” መሆናቸውን ተናገሩ

    ዶናልድ ትራምፕ የቻይናው ፕሬዝዳንት ዢ ጂንፒንግ "የሆርሙዝ ወሽመጥ ክፍት እና/ወይም በፍጥነት በመከፈቱ በጣም ደስተኛ ናቸው" ሲሉ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    ትራምፕ በቻይና ግንቦት 14 እና 15 የሚያደርጉት ስብሰባ እንደሚካሄድ እና "ልዩ እና ምናልባትም ታሪካዊ" እንደሚሆን ተናግረዋል።

    "ብዙ ነገር ይሳካል!"

    ቻይና ትልቋ የኢራን ነዳጅ ገዢ ስትሆን 38 በመቶ የሚሆነውን ነዳጇን የምታገኘው በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ በኩል ነው።

    ቻይና፣ ኢራን ከአሜሪካ ጋር እንድትደራደር በማሳሰብ ረገድ ወሳኝ ሚና ተጫውታለች። እንዲሁም የተኩስ አቁም ስምምነቱን እና የሰላም ድርድሩን እንደገና መጀመርን እንደምትደግፍ ትናገራለች።

  14. የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ የአሜሪካ እገዳ የሚቀጥል ከሆነ ሆርሙዝ “ክፍት ሆኖ አይቆይም” ሲሉ አስጠነቀቁ

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ ሞሐመድ ባጋር ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ ዶናልድ ትራምፕ “በአንድ ሰዓት ውስጥ ሰባት ነገሮችን ተናግረዋል፤ ሰባቱም ሐሰት ናቸው” ብለዋል።

    ጋሊባፍ “ጦርነቱን አላሸነፉም፤ በዚህ ውሸታቸው በድርድሮቹ የትም መድረስ እንደማይችሉ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል” ብለዋል።

    አፈ ጉባዔው ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ሲናገሩም “የአሜሪካ እገዳ ስለቀጠለ”፤ “እንደተዘጋ ይቆያል” ብለዋል።

    የአፈጉባዔው አስተያየት ከዚህ ቀደም በኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የተባለውን ያረጋገጠ ሆኗል።

    “ወሽመጡ ክፍትም ሆነ ዝግ የሚመራበት ደንብ የሚወሰነው መሬት ላይ እንጂ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ አይደለም” ብለው ነበር።

    ጋሊባፍ አስተያየታቸውን የሰጡት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በኤክስ ገጻቸው ላይ በእንግሊዘኛ የሆርሙዝ ወሽመጥ “በቀረው የተኩስ አቁሙ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ክፍት ነው” ካሉ በኋላ “ለሁሉም የንግድ መርከቦች ማለፍ ተፈቅዷል” ብለው ነበር።

    የአራጋቺ አስተያየት የተለያዩ ትችቶችን አስተናግዷል። የኢራን መገናኛ ብዙኃን እና ወግ አትባቂዎች ምን ማለታቸው እንደሆነ "ግልጽ" እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።

    ጋሊባፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ "የመገናኛ ብዙኃን ፐሮፖጋንዳ እና የሕዝብ አስተያየትን መቅረጽ የጦርነት አስፈላጊ አካል ናቸው፤ የኢራን ሕዝብ ግን በእነዚህ ስልቶች ተጽዕኖ አይደረግበትም" ብለዋል።

  15. በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ ጉዞ የኢራን አብዮታዊ ዘብ ፈቃድ እንደሚያስፈልገው ተዘገበ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በሆርሙዝ በኩል የሚያልፉ “ሁሉም የንግድ መርከቦች ሚያደርጉት ጉዞ ለቀሪው የተኩስ አቁሙ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ክፍት እንዲሆን መታወጁን” በኤክስ ገጻቸው አስታውቀው ነበር።

    የኢራን መንግሥት የቴሌቪዥን ጣቢያ አንድ “ከፍተኛ ወታደራዊ ባለሥልጣንን” ጠቅሶ ባስተላለፈው ዘገባ፤ የመርከቦቹ ጉዞ የሚከናወነው “በተለየ መስመር” እንደሆነ ገልጿል። መርከቦቹ ለማለፍ የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል ፈቃድ እንደሚያስፈልጋቸውም ጠቅሷል።

    ባለሥልጣኑ ለቴሌቪዥን ጣቢያው እንደተናገሩት፤ ይህ የተለየ የጉዞ መስመር የተወሰነው በኢራን የወደቦች እና ማሪታይም ድርጅት ነው።

    ጣቢያው ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣኑን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚደረግ የወታደራዊ መርከቦች ጉዞ አሁንም ቢሆን "የተከለከለ" ነው።

    በሌላ በኩል የመርከብ ጉዞ ኩባንያዎች የሆርሙዝ ደኅንነት እስከሚረጋገጥ ድረስ ወሽመጡን እንደማይጠቀሙ ተናግረዋል። ቢቢሲ ያነጋገረው አንድ የነዳጅ እና የጋዝ ጫኝ መርከቦች ኦፕሬተር፤ ለጊዜው የኢራን መግለጫ “ምንም የሚቀይረው ነገር የለም” ብሏል።

    “አላስፈላጊ አደጋ ውስጥ መግባት አለብን ብለን አናስብም፤ የኩባንያችን በወሽመጡ በኩል ቀድሞ የሚያልፍ ተቋም እንሆናለን የሚል አቋም የለውም” ሲል ገልጿል።

    በቀጣናው የሚገኙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ኦፕሬተር የሆነው ‘ስቴና በልክ’ የተሰኘው ኩባንያ በበኩሉ “ሁኔታውን በቅርበት እየተከታተለ” መሆኑን አስታውቋል።

    “የእያንዳንዱ ጉዟችን ውሳኔ የሚመሠረተው የሠራተኞቻችን እና የመርከቦቻችን ደኅንነት ላይ ነው፤ ደኅንነቱ የተጠበቀ መሆኑን እስካላረካን ድረስ ጉዞ አንጀምርም” ብሏል።

  16. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞ ላይ የተጣለው እገዳ እንደሚቀጥል አስታወቁ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ ከዚህ ሳምንት መጀመሪያ አንስቶ የወሰደችው ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞን የማገድ እርምጃ ቴህራን ስምምነት ላይ እስከምትደርስ ድረስ “በሙሉ ኃይል እና ተፈጻሚነት” እንደሚቀጥል ተናገሩ።

    ኢራን ዘግታ የቆየችውን የሆርሙዝ ወሽመጥ ለቀሪዎቹ የተኩስ አቁም ቀናት እንደምትከፍት አስታውቃለች።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለዚህ እርምጃ ምስጋና የሰጡበትን የትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጽ ጽሁፍ ከለጠፉ በኋላ ሌላ መልዕክት አጋርተዋል።

    ሆርሙዝ ቢከፈትም፤ “ከኢራን ጋር ያለን ጉዳይ 100% እስኪጠናቀቅ ድረስ በኢራን ላይ የተደረገው የባህር ኃይል እገዳ በሙሉ ኃይል እና ተፈፃሚነት ይቀጥላል" ብለዋል።

    "አብዛኛዎቹ ነጥቦች ድርድር የተደረገባቸው በመሆኑ ይህ ሂደት በጣም ፈጣን መሆን አለበት። ለዚህ ጉዳይ ለሰጣችሁት ትኩረት አመሰግናለሁ! ፕሬዝዳንት ዶናልድ ጄ. ትራምፕ" ሲሉ ውሳኔያቸውን አስታውቀዋል።

    አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚጓዙ ወይም ከዚያ የሚመጡ መርከች ላይ እገዳ የጣለቸው ሰኞ ዕለት ነበር።

    የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር በዚህ እርምጃ አማካኝነት ኢራን ከፔትሮኬሚካል ሽያጭ የምታገኘው በቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር እንዲቋረጥ የማድረግ ዓላማ አለው።

  17. ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ ለቀሪዎቹ የተኩስ አቁሙ ቀናት መከፈቱን አስታወቀች

    የሆርሙዝ ወሽመጥ “ለቀረው የተኩስ አቁም ጊዜ ሙሉ ለሙሉ ክፍት” እንደሚሆን የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ አስታወቁ።

    አራግቺ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ “ሊባኖስ ውስጥ በተደረሰው ተኩስ አቁም መሰረት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚደረግ የሁሉም የንግድ መርከቦች ጉዞ ለቀሪው የተኩስ አቁሙ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ክፍት እንዲሆን ታውጇል” ብለዋል።

    ለ40 ቀናት የተዋጉት አሜሪካ እና ኢራን በፓኪስታን አሸማጋይነት የሁለት ሳምንት ተኩስ አቁም መፈጸማቸው ይታወሳል። ይህ ተኩስ አቁም በሚቀጥለው ሳምንት ረቡዕ ይጠናቀቃል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ የመርከቦቹ ጉዞ የሚካሄደው “የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ የወደብ እና ማሪታይም ድርጅት አስቀድሞ ባሳወቀው የተቀናጀ መስመር” በኩል እንደሆነም ገልጸዋል።

    ለኢራን ውሳኔ ምላሽ የሰጡት አሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “አመሰግናለሁ” ሲሉ ትሩዝ ሶሻል በተባለው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ጽፈዋል።

    ትራምፕ፤ “ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ ክፍት መሆኑን እና ለሙሉ ጉዞ ዝግጁ መሆኑን አሁን አስታውቃለች። አመሰግናለሁ!" ብለዋል።

    የካቲት ላይ በአሜሪካ እና እስራኤል ጥቃት የተከፈተባት ኢራን ብዙ ከዓለም ነዳጅ ማጓጓዣ መስመሮች መካከል በርካታ መርከቦችን በማስተናገድ ቀዳሚ የሆነውን የሆርሙዝ ወሽመጥ ዘግታ ቆይታለች።

    ለዚህ እገዳ ምላሽ የሰጠችው አሜሪካ ደግሞ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ በወሽመጡ በኩል ወደ ኢራን ወደቦች ጉዞ እንዳይደረግ ከልክላለች።

  18. የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ሄዝቦላህ ላይ የተከፈተው ዘመቻ “አሁንም አልተጠናቀቀም” አሉ

    እስራኤል፤ ዳግም ውጊያ የሚጀመር ከሆነ ወደ መኖሪያቸው በመመለስ ላይ ያሉ በሺህዎች የሚቆጠሩ ንጹኃን ሊባኖሳውያን በድጋሚ ከደቡብ ሊባኖስ ሊፈናቀሉ እንደሚችሉ ማስጠንቀቋን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ (ኤኤፍፒ) ዘገበ።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ በቴሌቪዥን በተላለፈ መግለጫቸው፤ ሊባኖስ ውስጥ የተፈጸሙ ጥቃቶች “በርካታ ግቦችን ማሳካታቸውን” ተናግረዋል። ቢሆንም ግን ሄዝቦላህ ላይ የተከፈተው ዘመቻ “አሁንም እንዳልተጠናቀቀ” ገልጸዋል።

    “ዳግም ውጊያ ከተጀመረ ተልዕኮውን ለማጠናቀቅ እንዲቻል ወደ ደኅንነት ዞኑ የተመለሱት እነዛ ነዋሪዎች ለቅቀው መውጣት ይኖርባቸዋል” ብለዋል።

    የእስራኤል ጦር "አፅድቶ የተቆጣጠራቸውን" ቦታዎች በሙሉ ይዞ እንደሚቀጥል መናገራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ሄዝቦላህ የተኩስ አቁም ስምምነቱ ከተደረሰ በኋላ በሰጠው አስተያየት “"ማንኛውም የተኩስ አቁም በመላው የሊባኖስ ግዛት ሁሉን አቀፍ መሆን አለበት፤ ለጠላት እስራኤል ምንም ዓይነት የእንቅስቃሴ ነፃነት ሊፈቅድ አይገባም" ብሏል።

  19. የሄዝቦላህ አመራር ቡድኑ “መቼም ትጥቅ እንደማይፈታ” ለቢቢሲ ተናገሩ

    ሊባኖስ እና እስራኤል የደረሱት የ10 ቀን የተኩስ አቁም ስምምነት ከመጀመሩ አስቀድሞ ከቢቢሲ ጋር ቃለ መጠይቅ ያደረጉት የሄዝቦላህ ከፍተኛ አመራር ዋፊቅ ሳፋ ቡድን “መቼም፣ ጭራሽ” ትጥቅ እንደማይፈታ ገለጹ።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ ሄዝቦላህን ትጥቅ ማስፈታት በቀጣይ ከሊባኖስ መንግሥት ጋር ለሚደረግ ድርድር የተቀመጠ መሠረታዊ ጥያቄ መሆኑን ተናግረዋል።

    ስለ ትጥቅ መፍታት የተጠየቁት ሳፋ ግን “ተገቢ ተኩስ አቁም፣ ትክክለኛ የሆነ እስከሚደረስ አይደረግም" ብለዋል።

    "እስራኤል ለቅቃ እስካልወጣች ድረስ አይሆንም። እስረኞች ከመመለሳቸው፣ የተፈናቀሉ ሰዎች ወደ ቀያቸው ከመመለሳቸው እና መልሶ ግንባታ ከመጀመሩ በፊት ትጥቅ መፍታት አይኖርም። እስከዚያው ድረስ ስለ ሄዝቦላህ የጦር መሳሪያ ማውራት አይቻልም” ሲሉ ቅድመ ሁኔታዎቻቸውን ዘርዝረዋል።

    ቤይሩት ውስጥ በሚገኝ የመኖሪያ ሕንጻ ላይ የተደረገው ይህ ቃለ መጠይቅ በሄዝቦላህ እና በቀጣናዊ አጋሩ ኢራን መካከል ያለውን ቅንጅት ያሳያል። “ሄዝቦላህ እና ኢራን በአንድ ሰውነት ውስጥ ያሉ ሁለት ነፍሶች ናቸው” ብለዋል።

    “ያለ ኢራን ሄዝቦላህ ሊኖር አይችልም። ያለ ሄዝቦላህም አራን አትኖርም” ሲሉ በሁለቱ አካላት መካከል ስላለው “ሃይማኖታዊ፣ ሕጋዊ እና ርዕዮተ ዓለማዊ” ግንኙነት ገልጸዋል።

    የሺዓ እስልምና ፖለቲካዊ እና ወታደራዊ ቡድን የሆነው ሄዝቦላህ እንደ አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ እስራኤል እና በርካታ የዓለም አገራት በሽብርተኛ ድርጅትነት ተፈርጇል።

    ቡድኑ የአሁኑን የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት የተቀላቀለው የካቲት ላይ ወደ እስራኤል ሮኬቶችን ከተኮሰ በኋላ ነበር።

    ሄዝቦላህ ይህንን ጥቃት የፈጸመው በኢራን ጠቅላይ መሪ ላይ ለተፈጸመው ግድያ እንዲሁም ከህዳር 2016 ዓ.ም. አንስቶ እስራኤል በየቀኑ በሚባል ደረጃ ሊባኖስ ላይ ስትፈጽም ለነበረው ጥቃት በአጸፋ ምላሽነት መሆኑን ገልጿል።

    እስራኤልም ከፍተኛ የአየር ጥቃቶችን በመፈጸም እና ደቡባዊ ሊባኖስን በእግረኛ ወታደሮች በመውረር ምላሽ ሰጥታለች። ሄዝቦላህ ትጥቅ እስከሚፈታ ድረስም ይህንን ዘመቻ እንደምትቀጥል ተናግራለች።

    ሄዝቦላህ ቅድሚያ የሚሰጠው ለሊባኖስ ጥቅም ወይስ ለኢራን የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ሳፋ፤ “ያለ ምንም ጥርጥር ሄዝቦላህ የሚመለከተው የሊባኖስን ጥቅም ነው” ብለዋል።

    ኢራን ተኩስ አቁም ላይ እንዲደረስ ያሳደረችውን ግፊት ጨምሮ የምታደርጋቸው ድጋፎች ሊባኖስን ማገዛቸውን ጠቅሰዋል። ቢቢሲ ያነጋገራቸውን ጨምሮ በርካታ ሊባኖሳውያን ግን ቡድኑ ትጥቅ እንዲፈታ ይፈልጋሉ። አገሪቱን ግጭት ውስጥ ከትቷል ሲሉም ይወቅሳሉ።

    ሄዝቦላህ ትጥቅ ለመፍታት ፈቃደኛ ባለመሆኑ እና ሰፋ ያሉ ቅድመ ሁኔታዎችን በማስቀመጡ እንዲሁም እስራኤል የደኅንነት ጥያቄዎቿን አጥብቃ በመያዟ የተነሳ በሊባኖስ ተግባራዊ የሚሆን ማንኛውም ተኩስ አቁም ለረጅም ጊዜ የሚቆየውን ግጭት ለጊዜው ከመግታት ያለፈ ጥቅም ላይኖረው ይችላል።

  20. ኢራን የሊባኖስ ተኩስ አቁምን በበጎ እንደምትቀበለው ገልጻ ሄዝቦላህ ያደረገውን “ተጋድሎ” አወደሰች

    ኢራን በሊባኖስ የተደረሰውን የተኩስ አቁም ስምምነት ዲፕሎማሲያዊ ስኬት እና የሄዝቦላህ “ተጋድሎ” ውጤት እንደሆነ ገለጸች።

    ቴህራን የተኩስ አቁሙን የምትመለከተው በፓኪስታን አሸማጋይነት ከአሜሪካ ጋር የተደረሰው ሠፊ መግባባት አካል አድርጋ እንደሆነ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባቃኢ ተናግረዋል።

    ኢራን ሰፊ ቀጣናዊ የተኩስ አቁም እንዲደረስ ያለ ማቋረጥ ግፊት ስታደርግ መቆየቷንም በአጽንኦት አንስተዋል።

    የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ተኩስ አቁም ላይ ለመደረሱ ለሄዝቦላህ እውቅና ሰጥተዋል። የፓርላማ አፈ ጉባኤው ሞሐማድ ባገር ጋሊባፍ ኤክስ ገጻቸው ላይ በአረብኛ ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ስምምነቱ “የሄዝቦላህ የጽናት እና የአክሲስ ኦፍ ሬዚስታንስ የአንድነት ውጤት እንጂ ሌላ አይደለም” ብለዋል።

    አፈ ጉባኤው የጠቀሱት ‘አክሲስ ኦፍ ሬዚስታንስ’ ኢራን በቀጣናው ከሚገኙ አጋር ታጣቂ ቡድኖች ጋር የፈጠረችውን መረብ ለመግለጽ የምትጠቀምበት ስያሜ ነው።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ የኩስድ ኃይሎች አዛዥ የሆኑት ኢስማኢል ቃኒ በበኩላቸው ሄዝቦላህን “ባለ ድል” ሲሉ ጠርተዋል። ስምምነቱ የሊባኖስ የትግል ኃይሎች የጽናት እና የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ድጋፍ ውጤት መሆኑን ገልጸዋል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃንም የሊባኖስ ተኩስ አቁምን በተመለከቱ ዘገባዎቻቸው ያስተጋቡት የሄዝቦላህ “ተጋድሎ” እና የቴህራን ዲፕሎማሲያዊ ጫና ውጤት ነው የሚለውን የከፍተኛ ባለሥልጣናቱን አገላለጽ ነው።