ኦማን ከኢራን ጋር የሚደርገው ንግግር በጥሩ ሁኔታ እየሄደ ነው ስትል ቴህራን ወሽመጡ ወዲያውኑ አይከፈትም አለች

ኦማን ከኢራን ጋር በሆርሙዝ ወሽመጥ ዙሪያ የምታደርገው ንግግር በጥሩ ሁኔታ እየሄደ መሆኑን ስትገልጽ ቴህራን በበኩሏ ማንኛውም ስምምነት ወሽመጡን ወዲያውኑ እንዲከፈት ያደርጋል ማለት አይደለም ስትል አስጠነቀቀች። ሁለቱም አገራት ቅዳሜ ዕለት የሚደረገው ንግግር በጥሩ ሁኔታ እየሄደ መሆኑን ቢገልጹም ስምምነት መቼ እንደሚደረስ ግን ግልጽ አላደረጉም። የኦማን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመርከቦች ላይ የሚፈጸም ጥቃት ንግግሩ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር አስጠንቅቋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ደቡብ ኮሪያ በተደራጁ ወንጀሎች ላይ ለሦስት ወር የሚቆይ ዘመቻ ልትከፍት መሆኑን አስታወቀች

    የደቡብ ኮሪያ ፖሊስ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በደቦብ ኮሪያ ባለፉት ስድስት ወራት የተደራጁ እና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች መጨመራቸውን መረጃዎች ይጠቁማሉ።

    ደቡብ ኮሪያ በተደራጁ እና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች ላይ ሰኞ ዕለት ዘመቻ ልትጀምር መሆኗን አስታወቀች።

    ዘመቻው በወጣቶች በተደራጁ የወንጀል ቡድኖች ላይ የሚካሄድ ነው የተባለ ሲሆን በማጭበርበር፣ ሕገወጥ ገንዘብን ወደ ሕጋዊ መስመር በማስገባት ወንጀሎች ላይ እንደሚያተኩር የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የኮሪያ ብሔራዊ ፖሊስ ኤጀንሲ ዘመቻው እስከ ጥቅምት 21፣ 2019 ዓ.ም. እንደሚቆይ እና ከፍተኛ የፋይናንስ ወንጀሎች እንዲሁም የተደራጀ ሙስና፣ ሕገወጥ የግል አበዳሪዎች፣ የኦንላየን ቁማር ላይ እንደሚያተኩርም አስታውቋል።

    ፖሊስ በማኅበራዊ ሚዲያ አማካኝነት በሕገወጥ መልኩ የተገኘ ሀብት ያከማቹ ወንጀለኞችን ዒላማ እንደሚያደርግ ጨምሮ ገልጿል።

    የሌላ አገር ዜጎች የሚሳተፉበት የአደንዛዥ ዕጽ ንግድ ላይም ፖሊስ እርምጃ ለመውሰድ ካቀደባቸው ወንጀሎች መካከል ናቸው።

    በደቦብ ኮሪያ ባለፉት ስድስት ወራት የተደራጁ እና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች መጨመራቸውን መረጃዎች ይጠቁማሉ።

    ከመጋቢት እስከ ሰኔ ባሉት ወራት ውስጥ ብቻ ፖሊስ 1 ሺህ185 የወንጀል ቡድን አባላትን በቁጥጥር ሥር አውሏል።

    ከእነዚህም መካከል ዕድሜያቸው በ30ዎቹ ውስጥ የሆነ ወይም ከዚያ የሚያንሱ 63.6 በመቶ ይሆናሉ ተብሏል።

  2. ኢራን በአሸማጋዮች በኩል ከመነጋገር ባለፈ ከአሜሪካ ጋር ''በቀጥታ እየተደራደረች'' አለመሆኗን ገለጸች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ እሁድ ዕለት ቴህራን ከዋሽንግተን ጋር ቀጥተኛ ድርድር እያደረገች እንዳልሆነ እና በአሸማጋዮች በኩል ብቻ መልዕክቶችን መለዋወጧን ተናግረዋል።

    "ዩናይትድ ስቴትስ የመግባቢያ ስምምነቱን መጣስ እስክትተው እና ለጥሰቷ ካሳ እስካልከፈለች ድረስ ድርድሩን እንደገና ማስጀመር አይቻልም" ሲሉ አራግቺ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    “አሸማጋዮች አሁንም ድርድሩን ለማስጀመር አዳዲስ መንገዶችን ለመጠቀም እየሞከሩ ነው” ሲል አክለዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በየካቲት ወር ኢራንን ካጠቁ በኋላ የቀጣናው ውጥረት ተባብሷል።

    ቴህራን እና ዋሽንግተን በሚያዝያ ወር የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ የደረሱ ሲሆን በሰኔ ወር ደግሞ ወታደራዊ ግጭታቸውን ለማቆም እና ዘላቂ የሰላም ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።

    ይሁን እንጂ ስምምነቱ ባለፈው ወር ሁለቱ ወገኖች ለሁለት ሳምንታት ያህል አንዳቸው ሌላኛቸው ላይ ጥቃት በመፈጸማቸው ፈርሷል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግጭቱን ለመፍታት በሚደረጉ ውይይቶች ምክንያት ጦራቸው የሚፈጽመውን ድብደባ በድንገት አስቁመዋል።

  3. ሁቲዎች የሳዑዲ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ ጥቃት መፈፀማቸውን ገለጹ

    ጥቃቱን የሚያሳይ የሳተላይት ምስል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የኢራን አጋር የሆኑት ሁቲዎች በሳዑዲ አራምኮ ጃዛን ነዳጅ ማጣሪያ ላይ የፈጸሙትን ጥቃት የሚያሳይ የሳተላይት ምሥል

    የኢራን አጋር የሆኑት ሁቲዎች የሳዑዲ አራምኮ ጃዛን ነዳጅ ማጣሪያን እሁድ ዕለት ማጥቃታቸውን ተናገሩ።

    ሁቲዎች ጥቃቱን የፈጸሙት ሳዑዲ ከቱርክ እና ከፓኪስታን ጋር ወታደራዊ ትብብር ከፈረመች ከሁለት ቀናት በኋላ ነው።

    የሳዑዲ ኢነርጂ ሚኒስቴር በነዳጅ ማጣሪያው አካባቢ እሳት መቀስቀሱን ይፋ ካደረገ በኋላ በቁጥጥር ሥር መዋሉን ገልጿል።

    ነገር ግን እሳቱ በምን ምክንያት እንደተከሰተ ያለው ነገር የለም።

    የነዳጅ ማጣሪያው በደቡብ ምዕራብ ሳዑዲ አረቢያ የሚገኝ ሲሆን በቀን 400 ሺህ በርሜል ድፍድፍ ዘይት ያጣራል።

    በእሳት ቃጠሎው ስለደረሰው ውድመት የተባለ ነገር የለም።

    ሁቲዎች ማጣሪያውን ያጠቁት ድሮን ተጠቅመው መሆኑን ቃል አቀባያቸው ያህያ ሳሬ በኤክስ ገጻቸው ላይ አጋርተዋል።

    ኢራን እና አጋሯ የሆኑት የሁቲ ታጣቂዎች የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከተጀመረ በኋላ በሳዑዲ አረቢያ እና በሌሎች የባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ ጥቃት የሚፈጽሙ ሲሆን የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይም እገዳ ጥለዋል።

    የአራምኮ ኃላፊ የሆኑት አሚን ናስር ባለፈው ሳምንት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኩባንያው ተቋማት ላይ የሚደርሰው ጥቃት የምርት መስተጓጎል መፍጠሩን ተናግረው በፍጥነት ወደ ማምረት ተግባራችን እንመለሳለን ብለዋል።

    አራምኮ የዓለማችን ቀዳሚ ነዳጅ ላኪ ኩባንያ ነው።

    ኃላፊው አክለውም ጥቃቱ በቁስ ላይ ወይም በፋይናንስ ረገድ ያደረሰው ጉዳት የለም ብለዋል።

    የኢራን ጥቃት የዓለም የነዳጅ አቅርቦትን ካስተጓጎለ በኋላ አርብ ዕለት ሳዑዲ አረቢያ ከቱርክ እና ፓኪስታን ጋር ወታደራዊ ትብብር ተፈራርማለች።

    አገራቱ በዚህ ስምምነት መሠረት “ከሦስቱ አገራት በአንዱ ላይ የሚፈጸም ማንኛውም የትጥቅ ጥቃት በሁሉም ላይ እንደተፈጸመ ጥቃት ይቆጠራል" ብለዋል።

    አክለውም ይህ የጋራ ስምምነት "ማንኛውንም የጥቃት እርምጃ ለመከላከል የሚያስችል የጋራ የመከላከል አቅምን የማጠናከር” ዓላማ አለው ብለዋል።

  4. ፔንታጎን የጦር መሣሪያ አምራች ኩባንያዎች ምርታቸውን እንዲጨምሩ ግፊት እያደረገ መሆኑ ተገለጸ

    በኦክላሆማ ግዛት ሎተን አቅራቢያ በሚገኘው የፎርት ሲል የጦር ሰፈር ውጭ የሚታይ ተንቀሳቃሽ የፓትሪዮት ሚሳኤል ማስወንጨፊያ

    የፎቶው ባለመብት, AP

    የምስሉ መግለጫ, በኦክላሆማ ግዛት ሎተን አቅራቢያ በሚገኘው የፎርት ሲል የጦር ሰፈር ውጭ የሚታይ ተንቀሳቃሽ የፓትሪዮት ሚሳኤል ማስወንጨፊያ

    በኢራን ጦርነት ምክንያት የአሜሪካ ጦር መሣሪያ ክምችት መቀነሱ ከተዘገበ በኋላ ፔንታጎን የአገሪቱ የጦር መሣሪያ አምራች ኩባንያዎች በፍጥነት ምርታቸውን እንዲያሳድጉ ግፊት እያደረገ መሆኑ ተገለጸ።

    የፔንታጎን ቃል አቀባይ ሺን ፓርኔል ቅዳሜ ዕለት ባወጡት መግለጫ የመከላከያ መሥሪያ ቤቱ “ለተዋጊዎቻችን የሚያስፈልጉት የጦር መሳሪያዎች ስጋቱ በሚጠይቀው ፍጥነት” ቁጥሩን ለማሳደግ እየሰራ ነው ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ መሥሪያ ቤታቸው በፍጥነት የጦር መሣሪያዎቹ እንዲመረቱ እያደረገ መሆኑን አስታውቀው፤ ነገር ግን ይህ ከኢራን ጦርነት በፊት የተጀመረው ተቋሙን የማዘመን አካል ነው ብለዋል።

    የመከላከያ ምክትል ሚኒስትር የሆኑት ስቲቭ ፊንበርግ ረቡዕ ዕለት ለኩባንያዎቹ ኃላፊዎች በጻፉት እና “ዋሽንግተን ፖስት” በተመለከተው ደብዳቤ መሠረት “ወሳኝ ለሆኑ መሣሪያዎች እጅግ ፈጣን የሆነ የምርት መጨመርን የሚያረጋግጥ” ዕቅድ እንዲያቀርቡ ከ21 ቀናት ያልበለጠ ጊዜ ተሰጥቷቸዋል።

    ፊንበርግ “ረዥም ዓመት የሚወስድ የማበልጸጊያ ዑደት ተቀባይነት የለውም” ሲሉ በደብዳቤያቸው ላይ መጻፋቸው ተጠቅሷል።

    “የፕሮግራማችንን የጊዜ ሰሌዳ እጅግ በጣም ማፍጠን እና የምርት አቅማችንን አሁን ማሳደግ አለብን” ብለዋል ፊንበርግ።

    ምክትል ሚኒስትሩ ይህንን ደብዳቤ የጻፉት የአሜሪካ ወሳኝ ጦር መሣሪያዎች በአምስት ወሩ የኢራን ጦርነት መመናመናቸው ከተዘገበ በኋላ ነው።

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ሳምነት ወሳኝ የሚባሉ የጦር መሣሪያዎች ቁጥር መመናመኑን በተመለከቱ የወጡ ዘገባዎችን አጣጥለው “ከፍተኛ ቁጥር ያለው” መሣሪያ አለን ብለው ነበር።

    አክለውም “ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው መሣሪያዎች እየተመረቱ እና ወደ አሜሪካ እንደ አስፈላጊነቱ እየተጓጓዙ ነው” ብለዋል።

  5. ኦማን ንግግሩ በጥሩ ሁኔታ እየሄደ ነው ብትልም ቴህራን ወሽመጡ ወዲያውኑ እንደማይከፈት አስጠነቀቀች

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚያልፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኦማን ከኢራን ጋር በሆርሙዝ ወሽመጥ ዙሪያ የምታደርገው ንግግር በጥሩ ሁኔታ እየሄደ መሆኑን ስትገልጽ ቴህራን በበኩሏ ማንኛውም ስምምነት ወሽመጡን ወዲያውኑ እንዲከፈት ያደርጋል ማለት አይደለም ስትል አስጠነቀቀች።

    ሁለቱ አገራት ቅዳሜ ዕለት የሚደረገው ንግግር በጥሩ ሁኔታ እየሄደ መሆኑን ቢገልጹም ስምምነት መቼ እንደሚደረስ ግን ግልጽ አላደረጉም።

    የኦማን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመርከቦች ላይ የሚፈጸም ጥቃት ንግግሩ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር አስጠንቅቋል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ ውይይቱ የመጨረሻ ደረጃ ላይ መድረሱን የገለጹ ቢሆንም የወሽመጡ ዳግም መከፈት ግን “በሌሎች ቅድመ ሁኔታዎች ላይ የተመሠረተ ነው” ብለዋል።

    ቴህራን አሜሪካ እና እስራኤል በየካቲት ወር አጋማሽ ላይ ጥቃት ከፈጸሙባት በኋላ የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ የሚተላለፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ ዘግታለች።

    ከቅርብ ቀናት ወዲህ በኦማን እና በኢራን መካከል እየተካሄዱ ያሉ ንግግሮች ያተኮሩት በወሽመጡ ውስጥ አዲስ የመርከቦች መንቀሳቀሻ መስመር መክፈት ላይ ነው።

    በዚህ የባሕር መስመር ላይ ሁለቱም አገራት ኃላፊነት የሚኖራቸው ሲሆን ስምምነት ከተፈረመ መርከቦች ያለ ችግር መንቀሳቀስ እንዲችሉ ያደርጋል ተብሏል።

    ነገር ግን አራጋቺ የወሽመጡ ዳግም ሙሉ በሙሉ መከፈት የሚወሰነው ሌሎች ቅድመ ሁኔታዎች ሲሟሉ ነው ብለዋል።

    እነዚያ ቅድመ ሁኔታዎች ምን መሆናቸውን በሚመለከት ግን የሰጡት አጭር ማብራሪያ ብቻ ነው።

    አራጋቺ አሜሪካ በሰኔ ወር የተደረሰውን ስምምነት በመጣሷ ካሳ መክፈል ይኖርባታል ብለዋል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል በሰኔ ወር የተፈረመው የመግባቢያ ሰነድ ወዲያውኑ የፈረሰ ሲሆን ዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችም ተቋርጠው ለቀናት የተኩስ ልውውጥ ሲደረግ ቆይቷል።

    የኢራን የደህንነት ኃላፊ ሞሐማድ ባጋር ዞልቃድር ደግሞ በሌላ መግለጫ ላይ አሜሪካ ባህሪዎን “እስክታስተካክል ድረስ” የሆርሙዝ ወሽመጥ አይከፈትም ብለዋል።

    ኃላፊው አክለውም አሜሪካ ስድስት የኢራን ቅድመ ሁኔታዎችን ማሟላት አለባት ካሉ በኋላ ኢራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት እና ዛቻ ማቆም፣ ወደቦቿ ላይ የጣለችውን እገዳ ማንሳት፣ የታገዱ የኢራን ሃብቶች መልቀቅ እንደሚገኙባቸው ጠቅሰዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ከኢራን ጋር “በቅርቡ” ስምምነት ይደረሳል ብለው የነበረ ቢሆንም ምክትላቸው ጄዲ ቫንስ ግን ቅዳሜ ዕለት የሚቀሩ ነገሮች እንዳሉ በመግለጽ ጥርጣሬያቸውን ለፎክስ ኒውስ ተናግረዋል።

  6. የኢራን አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ ሁሉንም ቅድመ ሁኔታዎች ሳትቀበል ሆርሙዝ አይከፈትም አለ

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የሆርሙዝ ወሽመጥ የመከፈቱ ጉዳይ የሚወሰነው አሜሪካ ከቴህራን የቀረቡላትን ቅድመ ሁኔታዎች በሙሉ ስትቀበል ብቻ እንደሆነ ገለጸ።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ በበኩላቸው ሆርሙዝን በተመለከተ ከኦማን ጋር የሚደረገው ድርድር እየተጠናቀቀ ቢሆንም፣ ይህ ስምምነት ወሽመጡ ይከፈታል ማለት እንዳልሆነ ተናግረዋል።

    በሆርሙዝ ሁለት ጫፎች የሚገኙት ኢራን እና ኦማን ወሽመጡ የሚተዳደርበትን መንገድ በተመለከተ ሲደራደሩ ቆይተዋል። ይህ ድርድር ወደ መቋጫው መቃረቡን ተከትሎም፣ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ሆርሙዝ መከፈቱ “አይቀሬ” እንደሆነ መናገራቸው ተዘግቧል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አራግቺ፣ “የሆርሙዝ ወሽመጥን ሕጋዊ መዋቅር፣ አስተዳደር እና የመርከብ ጉዞ መስመርን ለመወሰን” የሚደረገው ድርድር “ለስምምነትም መቃረቡን” ዛሬ ቅዳሜ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ከኦማን ጋር ስምምነት መፈጸሙ ግን የወሽመጡን መከፈት እንደማያረጋግጥ ጠቁመዋል። “የሆርሙዝ መከፈት በሌሎች ሁኔታዎች ላይ የሚመሰረት ነው” ብለዋል። “አሜሪካ የኢስላማባድ የመግባቢያ ስምምነትን በመጣሷ ካሳ እንድትከፍል ማድረግ” ከቅድመ ሁኔታዎቹ አንዱ እንደሆነ ጠቅሰዋል።

    በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየት የሰጡት የኢራን እስላማዊ አብዮት ዘብ ቃል አቀባይ ጄኔራል ሆሴይን ሞሄቢም በተመሳሳይ ኦማን ጋር የሚደረገው ድርድር ከሆርሙዝ መከፈት ጋር ግንኙነት እንደሌለው ገልጸዋል።

    ቃል አቀባዩ “ሆርሙዝ ወሽመጥ ለእኛ ኢኮኖሚያዊ የውሃ መስመር ብቻ አይደለም። በእስላማዊው ሪፐብሊክ እጅ የሚገኝ ጂኦግራፊያዊ አቅም እና ጉልበት ጭምር ነው። ስለዚህ ጠላት ወሽመጡ እንዲከፈት የኢራንን ቅድመ ሁኔታዎች ለመቀበል ይገደዳል” ብለዋል።

    አክለውም፤ “የአሜሪካ ወገን የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክን ቅድመ ሁኔታዎች ሲቀበል እና ጣልቃ የመግባት አካሄዱን ሲተው፣ ሆርሙዝ ወሽመጥን እንደገና ለመክፈት የሚያስችሉ ሁኔታዎች ይኖራሉ” ብለዋል።

  7. የቀድሞው የትራምፕ ጠበቃ የአሜሪካ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ሆነው ተሾሙ

    ቶድ ብላንች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የቀድሞ የግል ጠበቃ ቶድ ብላንች በአሜሪካ ከፍተኛው የሕግ አስከባሪ ኃላፊነት በሆነው ጠቅላይ አቃቤ ሕግነት እንዲሰሩ የተሰጣቸው ሹመት በሴኔት ጸደቀ።

    በ50 ለ49 በሆነ ድምፅ ሹመታቸው የጸደቀላቸው ብላንች፣ ከሪፐብሊካቹ ሴናተሮች ሱዛን ኮሊንስ እና ሊዛ ሙርኮውስኪ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።

    ሹመታቸው እንዲጸድቅ ያስቻለውን ወሳኝ ድምፅ የሰጡት ሴናተር ቢል ካሲዲ ናቸው። ትራምፕ እና ካሲዲ ለዓመታት የዘለቀ አለመግባባት ውስጥ ስለነበሩ የሴናተሩ ውሳኔ ተጠባቂ ነበር።

    ሴናተሩ፣ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሊያቀርቡ ከሚችሏቸው ዕጩዎች መካከል የተሻለው ናቸው ብለው እንደሚያምኑ በመግለጽ ድጋፋቸው ሰጥተዋል።

    ይህ ውሳኔ፣ በጊዜያዊ አቃቤ ሕግነት ሲሰሩ በቆዩት ብላንች ምክንያት ሴኔት ውስጥ በሚገኙ ሪፐብሊካኖች እና በትራምፕ አስተዳደር መካከል ከሚያዝያ አንስቶ የተፈጠረውን መፋጠጥ የቋጨ ሆኗል።

    የሴኔት አባል የሆኑ ዴሞክራቶች በሙሉ ፍትሕ መስሪያ ቤቱን እንዲመሩ የቀረቡትን እጩ በመቃወም ድምፅ ሰጥተዋል።

    የተወሰኑ ሪፐብሊካኖች፣ ከወሲብ ወንጀለኛው ጄፍሪ ኤፕስቲን ጋር የተያያዙ ሰነዶች በፍትሕ መስሪያ ቤቱ የተለቀቁበትን መንገድ በተመለከተ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

    ቶድ ብላንች የትራምፕን የ1.8 ቢሊዮን ዶላር "የፀረ መሣሪያነት" ፈንድ በማቋቋ ረገድ የነበራቸውን ሚናም አንስተዋል።ይህ ፈንድ በመንግሥት መሳደድ እንደደረሰባቸው ለሚገልጹ ሰዎች ካሳ ለመክፈል ያቀደ ነው።

    ነገር ግን እንደ የሴኔት አባሏ ሊዛ ሙርኮውስኪ ተቺዎች፣ ፈንዱ በ2020 ትራምፕ በምርጫ ከተሸነፉ በኋላ በኮንግረስ ላይ በተፈጸመው አመጽ ተሳታፊ ስለሆኑ ክስ ለተመሰረተባቸው ሰዎችም ሊሰጥ ይችላል የሚል ስጋት አላቸው።

    ብላንች ሹመታቸው እንዲጸድቅ ለሴኔት በቀረበበት ወቅት ይህ እቅድ ከፍተኛ ተቃውሞ ተነስቶበታል። ይህንን ተከትሎም አዲሱ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ እቅዱን እንዲቀር አድርገዋል።

  8. ሩሲያ በዩክሬን መዲና አቅራቢያ በፈጸመችው የሚሳዔል ጥቃት ሕጻን ልጅን ጨምሮ ሦስት ሰዎች ተገደሉ

    በእሳት የተያያዙ ቤቶች

    የፎቶው ባለመብት, Ukraine state emergency service DSNS

    የሩሲያ ጦር አርብ ምሽት በዩክሬን ዋና ከተማ ኪዬቭ አቅራቢያ በፈጸመው የሚሳዔል ጥቃት አንድ ሕጻንን ጨምሮ ቢያንስ ሦስት ሰዎች መገደላቸውን የአካባቢው ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    የአሁኑ ድብደባ የተካሄደው፣ 21 ሰዎች የተገደሉበት ጥቃት በመላው ዩክሬን ከተፈጸመ ከጥቂት ቀናት በኋላ ነው።

    በትናንቱ ጥቃት የሩሲያ ሚሳዔሎች በዋና ከተማዋ በስተምሥራቅ የሚገኝ ስፍራን የመቱ ሲሆን፣ የኃይለኛ ፍንዳታ ድምጽ መሰማቱንም እማኞች ተናግረዋል።

    የባሊስቲክ ሚሳዔል ጥቃቱ የሦስት ሰዎችን ሕይወት እንደቀጠፈ እና ሌሎች ሦስት ሰዎችን እንዳቆሰለ የአካባቢው ወታደራዊ አስተዳደር ኃላፊ ተናግረዋል።

    የሚሳዔል ስብርባሪዎች በመኖሪያ ሕንፃዎች እና ተሽከርካሪዎች ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን እንዲሁም አንድ ሕንጻ ላይ እሳት ማስነሳታቸውንም ገልጸዋል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ኪዬቭ ውስጥ ሕንጻ እና የነዳጅ ማጠራቀሚያ ላይ የተነሳን እሳት ለማጥፋት እየተረባረቡ መሆኑን የከተማው ከንቲባ በቴሌግራም ገጻቸው አስታውቀዋል።

    የዩክሬን የድንገተኛ አደጋ አገልግሎት በበኩሉ በዋና ከተማዋ የሚገኙ ጋራጆች፣ የንግድ ተቋም እና ሕንፃ በእሳት ተያይዘው የሚያሳዩ ምስሎችን አጋርቷል። ምን ያህል ሰዎች እንደተጎዱ እየተጠራ መሆኑም አክሏል።

    ይህ ጥቃት የተፈጸመው ዩክሬን ወደ ሩሲያ ድንበር ጠልቃ በመግባት የአገሪቱን ሁለት ነዳጅ ማጣሪያዎች ከመታች በኋላ ነው። ከሩሲያ ጋር ግንኙነት ያለው መርከብ ላይ ጥቃት አድርሳለች።

    የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ፕሬዚዳንት ቮሎዲሚር ዘሌንስኪ ለመጀመሪያ ጊዜ በሰርቢያ ለሚያደርጉት ጉብኝት ዋና ከተማዋ ቤልግሬድ ገብተዋል።

    በቆይታቸው ከሰርቢያው ፕሬዚዳንት አሌክሳንደር ቩቺች ጋር ተገናኝው ስለ ኢኮኖሚያዊ ትስስር፣ የደኅንነት ጉዳዮች እና ከአውሮፓ ህብረት ጋር ስላለው ግንኙነት እንደሚጋገሩ ይጠበቃል።

    ዜሌንስኪ ዩክሬን ሠፊ ድጋፍ እንድታገኝ እየጠየቁ ቢሆንም የሰርቢያው ፕሬዝዳንት ሩሲያ ላይ ማዕቀቦችን ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኛ አልሆኑም።

    ሰርቢያ የአውሮፓ ኅብረትን ለመቀላቀል እየሞከረች ሲሆን ለዩክሬን እርዳታ አቅርባለች። ከጦርነቱ በኋላ በሚኖረው አገሪቱን መልሶ የመገንባት እንቅስቃሴ እገዛ ለማድረግም ቃል ገብታለች።

  9. የኢራን ፕሬዝዳንት “መብቶቻችንን በንግግር ማስከበር እየቻልን ለምን እንዋጋለን?” አሉ

    ፕሬዝዳንት መስኡድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Irna

    ከየካቲት አንስቶ ከአሜሪካ ጋር ጦርነት ውስጥ ያለችው ኢራን ፕሬዝዳንት የሆኑት መስኡድ ፔዜሽኪያን፣ “መብቶቻችንን በንግግር ማስከበር እየቻልን ለምን እንዋጋለን?” ሲሉ በሁለቱ አገራት መካከል ለሚደረገው ድርድር ያላቸውን ድጋፍ ገለጹ።

    ቴህራን ከያዘቻቸው አቋሞች ፈቀቅ እንደማትል የገለጹት ፕሬዝዳንቱ፣ የጦርነቱ መቀጠል ግን “ኢራን እጅ እድትሰጥ” የምትፈልገው እስራኤል እንድንከተል የምትሻው መንገድ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    አምስት ወር ያለፈው የመካከለኛው ምሥራቅ ግጭትን በድርድር ለመፍታት የተደረጉ ጥረቶች እስካሁን ድረስ ይሄ ነው የሚባል ውጤት አላስገኙም።

    ሁለቱ አገራት ባለፈው ሰኔ ላይ በቀጣይ ጦርነቱን የሚቋጭ ድርድር ለማድረግ የሚያስችላቸውን ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ስምምነት ተፈራርመው የነበረ ቢሆንም በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ጥቃት ወደመፈጸም ተመልሰዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሰሞኑ ከኢራን ጋር ድርድር እየተካሄደ መሆኑን በተደጋጋሚ ሲናገሩ ቢደመጡም፣ ቴህራን ለንግግር የመቀመጥ ዕቅድ እንዳልያዘች በመግለጽ ጭምር አስተባብላለች።

    ትናንት አርብ ወደ ሥልጣን የመጡበትን ሁለተኛ ዓመት ክብረ በዓልም አስመልክቶ ባስተላለፉት መልዕክት ፕሬዝዳንት መስኡድ ፔዜሽኪያን፣ ኢራን በንግግር አማካኝነት የሊባኖስን ጦርነት ማስቆም፣ የተጣለውን እገዳ ማስነሳት እና የተወሰኑ ማዕቀቦችን እንዲላሉ ማድረግ መቻሏን ጠቅሰዋል።

    ኢራን በንግግር አማካኝነት ብሔራዊ ጥቅሞቿን ለማስጠበቅ ዝግጁ መሆኗን ያነሱት ፕሬዝዳንቱ፣ ሉዓላዊነቷን ወይም የመከላከል አቅሟን አደጋ ላይ የሚጥሉ ጥያቄዎችን እንደማትቀበል መናገራቸውን የአገሪቱ መንግሥት የዜና ወኪል የሆነው ‘ኢርና’ ዘግቧል።

    ፔዜሽኪያን በንግግራቸው፤ ድርድርን በተመለከተ በአገሪቱ አመራር መካከል ተፈጥሯል ስለተባለው መከፋፈልም ጠቅሰዋል።

    የፕሬዝዳንቱ አስተደዳር የአገሪቱ አመራር ድርድር እንዲቀበል ጫና አድርጓል መባሉን ውድቅ ያደረጉት ፔዜሽኪያን፣ ዋና ዋና ውሳኔዎች የተላለፉት በአመራሩ ይሁንታ እና ቅንጅት እንደሆነ ተናግረዋል።

    አክለውም፣ ዲፕሎማሲ ከኢራን የመከላከያ ጥንካሬ ጋር የማይጣጣም ተደርጎ መታየት እንደሌለበት በማንሳት ተከራክረዋል።

    ድርድር የኢራንን መብቶች እና ጥቅሞችን ለማስከበር ጠቃሚ ሊሆን እንደሚችል ገልጸዋል። ይሁን እንጂ የኢራንን ወታደራዊ እና የመከላከል አቅም ለመበተን የሚቀርቡ ጥያቄዎች ተቀባይነት እንደማይኖራቸው ተናግረዋል።

  10. ሳዑዲ አረቢያ፣ ቱርክ እና ፓኪስታን አንዳቸው ላይ የሚፈጸም ጥቃትን የሚመክቱበት ወታደራዊ ስምምነት ተፈራረሙ

    የሳዑዲ ዓረቢያው አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ሰልማን፣ የቱርኩ ፕሬዚዳንት ረሲፕ ታይፕ ኤርዶጋን እና የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሸሪፍ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሳዑዲ አረቢያ፣ ቱርክ እና ፓኪስታን በአንዳቸው ላይ የሚፈጸም ጥቃት በሦስቱም ላይ የተከፈተ ሆኖ እንደሚቆጠር የሚገልጽ ወታደራዊ ስምምነት ተፈራረሙ።

    ስምምነቱ ይፋ የሆነው የሳዑዲ ዓረቢያው አልጋ ወራሽ መሐመድ ቢን ሰልማን፣ የቱርኩ ፕሬዚዳንት ረሲፕ ታይፕ ኤርዶዋን እና የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሸሪፍ በሳዑዲ ዓረቢያዋ መካ ከተማ በተካሄዱት ስብሰባ ላይ ነው።

    ሦስቱ አገራት ወታደራዊ አጋርነታቸውን ያጠናከሩት አሜሪካ እና ኢራን የሚያደርጉት ጦርነት ሳዑዲ ዓረቢያ ጎትቶ ባስገባት በዚህ ወቅት ነው።

    ወሳኝ የነዳጅ መጓጓዣ በሆነው ሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲሁም በቀይ ባሕር በኩል የሚደረጉ የመርከቦች ጉዞዎችም መስተጓጎል ውስጥ ናቸው።

    ሳዑዲ ዓረቢያ እና ፓኪስታን ባለፈው ዓመትም ተመሳሳይ የጋራ የመከላከያ ስምምነት መፈጸማቸው አስታውቀው ነበር።

    አሁን የተፈረመው የመካ የጋራ የመከላከያ ስምምነት "ማንኛውንም የጥቃት እርምጃ ለመከላከል የሚያችል የጋራ የመከላከል አቅምን የማጠናከር” ዓላማ አለው።

    ያወጡት መግለጫ “ከሦስቱ አገራት በአንዱ ላይ የሚፈጸም ማንኛውም የትጥቅ ጥቃት በሁሉም ላይ እንደተፈጸመ ጥቃት ይቆጠራል" ይላል።

    በተጨማሪም ስምምነቱ "በሦስቱ አገራት መካከል የሚኖሩ የመከላከያ ትብብር ዘርፎችን በሙሉ ያሳድጋል” ብለዋል።

    ስምምነቱ በሦስቱ የሱኒ እስልምና ተከታይ አገራት አንዳቸው ለሌላቸው እገዛ እንደሚያቀርቡ ቢገልጽም፤ የእያንዳንዱ አገር የሚኖርበትን ግዴታ አልዘረዘረም።

    ሮይተርስ በዘገባው የጠቀሳቸው አንድ የቱርክ ባለሥልጣን፣ ስምምነቱ "በባህሪው የመከላከል ብቻ” እንደሆነ ገልጸዋል።

    ሳዑዲ አረቢያ ያላትን ከፍተኛ ፋይናንስ አቅም ለዚህ የመከላከያ ትብብር ታቀርባለች። በተጨማሪም ሳዑዲ በከፍተኛ መጠን መሣሪያ ከሚገዙ አገራት አንዷ ነች።

    በኔቶ ጥምረት ውስጥ ከፍተኛ ወታደራዊ ኃይል በመያዝ ሁለተኛ የሆነችው ቱርክ ደግሞ ዘመናዊ የመከላከያ መሣሪያዎችን የማምረት አቅም አላት። ሦስተኛዋ ተፈራራሚ አገር ፓኪስታን በአንጻሩ የኒውክሌር መሣሪያን ታጥቃለች።

    ሦስቱ አገራት፣ የኢራን ጦርነት የመቋጨት ምልክት እያሳየ ባለመሆኑ እንዲሁም አሜሪካ ጦርነቱ ያስከተለውን የቀጣናዊ ተፅዕኖውን መቆጣጠር አለመቻሏን በመጥቀስ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

    የአሸማጋይነት ሚናን የያዘችው ፓኪስታን፤ አሜሪካ እና ኢራን ያደረጓቸውን የተኩስ አቁም ድርድሮች አስተናግዳለች።

    ሳዑዲ ራሷን ከግጭቱ ውጪ አድርጋ ብትቆይም፣ ሦስት አቅጣጫ ከደረሰባት ምት በኋላ ባለፈው ወር ላይ ከአሜሪካ ጋር በመሆን ኢራቅ ውስጥ የሚገኙ የኢራን ተቀጽላ ታጣቂዎች ላይ ጥቃት ፈጽማለች።

    በተጨማሪም ባለፈው ወር የየመኖቹ ሁቲዎች ሳዑዲ ላይ “የባሕር ጉዞ ማዕቀብ” መጣላቸውን ያሳወቁ ሲሆን፣ በአገሪቱ አየር ማረፊያዎች፣ የነዳጅ መሠረተ ልማቶች እና በቀይ ባሕር ሲጓዝ የነበረ ነዳጅ ጫኝ መርከብ ላይ ጥቃት ፈጽመዋል።

    ሳዑዲ አረቢያም በሁቲ ይዞታዎች ላይ ጥቃት በማድረስ አጸፋውን መልሳለች።

  11. ኤርትራ የ2026 የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ማኅበራዊ ፎረም ሊቀመንበር ሆና መሾሟን ዩኤን ዎች አወገዘ

    በተመድ የኤርትራ ቋሚ ተልዕኮ ጉዳይ አስፈጻሚ የሆኑት ሀብቶም ዘርአይ የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ማኅበራዊ ፎረም ሊቀመንበር ሆነው ተሾመዋል

    የፎቶው ባለመብት, UN

    የምስሉ መግለጫ, በተመድ የኤርትራ ቋሚ ተልዕኮ ጉዳይ አስፈጻሚ የሆኑት ሀብቶም ዘርአይ የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ማኅበራዊ ፎረም ሊቀመንበር ሆነው ተሾመዋል

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንቅስቃሴዎችን የሚከታተለው ዩኤን ዎች ኤርትራ የ2026 የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ማኅበራዊ ፎረም ሊቀመንበር ሆና መሾሟን አወገዘ።

    ተቋሙ ውሳኔውን “በዓለም ላይ ካሉ እጅግ አፋኝ አምባገነናዊ ሥርዓቶች አንዱን ሰብዓዊ መብቶችን የማሳደግ ኃላፊነት ያለበት አካል ኃላፊ ማድረግ አስነዋሪ ቀልድ ነው” ሲል ትናንት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

    በመግለጫው፣ በከባድ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የሚከሰሱ ሰዎች፣ ዋና ዓላማው ሰብዓዊ መብቶችን መጠበቅና ማሳደግ የሆነ ተቋምን እንዲመሩ እየተደረገ ነው ሲሉ የዩኤን ዎች ዋና ዳይሬክተር ሂሌል ኖየር ገልፀዋል።

    በትግራይ ጦርነት ወቅት የኤርትራ ወታደሮች በሰሜን ኢትዮጵያ ክፍል አጎራባች አካባቢዎች ላይ ወረራ በማካሄድ፣ በመድፈር እና ንብረት በመዝረፍ ተሳትፈዋል በሚል ክስ አሜሪካ በኤርትራ ላይ ማዕቀብ እንደተጣለባት መግለጫው አስታውሷል።

    የኤርትራ መንግሥት ዜጎቹን የብሔራዊ አገልግሎት እንዲሰጡ የሚያስገድድ፣ ተቃዋሚዎችን እና ጋዜጠኞችን ያለ ፍርድ ለዓመታት የሚያስር እና የሃይማኖት ጭቆና የሚያሳድር ነው ሲልም መግለጫው አስፍሯል።

    “ይህ፣ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት የራሱን መመዘኛዎች በማክበር ረገድ የሚያሳየው ሥር የሰደደ ውድቀት የቅርብ ጊዜ ማሳያ ነው” ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ምክር ቤቱ በተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚፈጽሙ አካላት ተፅዕኖ የሚፈጥሩ ቦታዎችን እንዲይዙ ፈቅዷል ብለዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንቅስቃሴዎችን የሚከታተለው ዩኤን ዎች

    የፎቶው ባለመብት, UN Watch

    ኖየር ይህ ድርጊት የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብት አጠባበቅ ሥርዓት አጠቃላይ ተዓማኒነት ይበልጥ ይሸረሸራልም ሲሉ አክለዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት ሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ቮልከር ቱርክ ይህንን ሹመት ያለምንም መዘግየት በይፋ እንዲያወግዙ እንጠይቃለን ሲሉ ዋና ዳይሬክተሩ ጥሪ አቅርበዋል።

    በተጨማሪም በተለይም እንደ ፈረንሳይ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ኔዘርላንድስ፣ ጣሊያን፣ ስፔን፣ ብራዚል፣ ጃፓን እና ስዊዘርላንድ ያሉ የተባበሩትመንግሥታትድርጅትየሰብዓዊመብቶችምክርቤት አባል ሀገራት የኤርትራን ሊቀመንበርነት የሚቃወም አፋጣኝ የጋራ መግለጫ እንዲያወጡ እንጠይቃለን ብለዋል።

    እነዚህ መንግሥታት ይህንን ሹመት እንዲሻር መጠየቅ እና በኤርትራ አመራር ሥር የሚካሄዱ ማንኛውንም ሂደቶች ህጋዊነት እንደማይሰጡ ማሳወቅ አለባቸው ሲሉም ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።

    በፈረንጆቹ ጥቅምት 29 እና 30 ቀን 2026፣ በጄኔቫ በሚካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ማኅበራዊ ፎረም “ዓለም አቀፍ ትብብርንና አንድነትን” ማሳደግ ላይ ትኩረት ያደረገ ነው።

  12. ቱርክ፣ ሳዑዲ አረቢያ እና ፓኪስታን ወታደራዊ ስምምነት ሊፈራረሙ ነው

    የሳዑዲ አረቢያ፣ ቱርክ፣ እና ፓኪስታን ባንዲራዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ቱርክ፣ ሳዑዲ አረቢያ እና ፓኪስታን የሦስትዮሽ ወታደራዊ ስምምነት ሊፈራረሙ መሆኑን ወታደራዊ ምንጮች ገለጹ።

    ሦስቱ አገራት የጋራ ወታደራዊ ስምምነት የሚፈራረሙት በሳዑዲ ከተማ ጂዳ መሆኑን ምንጮቹ ጨምረው ገልጸዋል።

    የቱርክ ፕሬዚዳንት ረሲፕ ጣይብ ኤርዶዋን አርብ ማለዳ ወደ ሳዑዲ አረቢያ ለአንድ ቀን ጉብኝት አቅንተዋል። የፓኪስታኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ጂዳ የደረሱት ሐሙስ ዕለት መሆኑ ታውቋል።

    ፕሬዚዳን ኤርዶዋን ከሳዑዲ ልዑል ሞሐመድ ቢን ሳልማን ጋር እንዲሁም ከፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ ጋር ተገናኝተው ይወያያሉ ተብሏል።

    ፓኪስታን በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የሰላም ስምምነት እንዲደረስ የምታሸማግል ሲሆን ቱርክ ደግሞ የጋዛ የተኩስ አቁም እንዲፈረም ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ስታደርግ ነበር።

    ስምምነቱ ሁሉንም ወታደራዊ ትብብሮች እንደሚያካትት ተገለጿል።

    ፓኪስታን እና ቱርክ ከፍተኛ ጦር መሣሪያ እና ላኪ አገራት ናቸው።

  13. በኮንጎ በኢቦላ ቫይረስ መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች ቁጥር ከ4000 በላይ መሆኑ ተገለጸ

    የሕክምና ባለሙያዎች ጭምብል ለብሰው

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በኢቦላ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 4,053 መድረሱ ሲረጋገጥ 1850 ሰዎች ደግሞ መሞታቸው ታውቋል።

    በኮንጎ የተከሰተው ኢቦላ በፍጥነት በመዛመት በዓለማችን ሁለተኛው ግዙፍ ወረርሽኝ ሆኖ ተመዝግቧል።

    ባለሙያዎች ወረርሽኝ መከሰቱ እአአ ግንቦት 15 በይፋ ከመነገሩ ከወራት በፊት እንደተከሰተ ያምናሉ።

    በዚህም የተነሳ በኢቦላ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር በይፋ ከተገለጸው የሚበልጥ ሊሆን አንደሚችል ተናግረዋል።

    የማዕከላዊ አፍሪካ የኅብረተሰበ ጤና ኢንስቲትዩት በአጠቃኣይ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 4,053 መሆኑን ገለጾ 1850 ሞተዋል ብሏል።

    ይህ መረጃ የተሰበሰበው በአገሪቱ ከሚገኙት አምስት ግዛቶች ነው።

    በሳይንስ ጆርናል ላይ የታተመ ሪፖርት ወረርሽኙ በኢቱሪ ግዛት የጀመረው በጥር ወር ወይንም ከዚያ ቀደም ብሎ ሊሆን እንደሚችል ይገልጻል።

    በጥር ወር አጋማሽ እና ግንቦት 15 መካከል በቫይረሱ የተያዙ 500 ሰዎችን መለየታቸውን ባለሙያዎች ተናግረዋል።

    ዘግይቶ ወረርሽኝ መከሰቱ መታወቁ፣ በአገሪቱ ያለው የትጥቅ ግጭት፣ እና የክትባት እና የሕክምና አለመኖር ወረርሽኙን ለመቆጣጠር አስቸጋሪ አድርጎታል።

    ወረርሽኙ ከዚህ ቀደም ከ2018 እስከ 2020 ከተነሳው አንጻር የከፋው እንደሆነ ተገልጿል። በያዝነው ዓመት ወረርሽኙ መነሳቱ በይፋ የተገለጸው ግንቦት 15 ነበር።

    አሁን ላይ ለቡንዲቡግዮ ዝርያ ፈቃድ የተሰጠው ክትባት የለም። ሆኖም በዩናይትድ ኪንግደም እና ሲንጋፖር ክትባቶች እየተሠሩ ነው።

    ወረርሽኙ የተነሳው በሰሜን ምሥራቅ ኢቱሪ ግዛት ሲሆን፤ አካባቢው ከደቡብ ሱዳን እና ኡጋንዳ ጋር ይዋሰናል።

    ወረርሽኙ ወደ ሰሜናዊ የአገሪቱ ክፍል እና ወደ ደቡብ ኪቩ ግዛቶችም ተስፋፍቷል። እነዚህ አካባቢዎች በአመዛኙ በኤም23 ቁጥጥር ሥር ናቸው።

  14. የኢራን ፓርላማ አሜሪካ እና እስራኤል በሆርሙዝ ወሽመጥ እንዳያልፉ የሚከለክል ረቂቅ ሕግ አቀረበ

    የሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚቀዝፉ መርከቦች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን ፓርላማ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል እና በፐርዢያ ባሕረ ሰላጤ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ላይ ያለውን ቁጥጥር የሚያጠብቅ ረቂቅ ሕግ ላይ ተወያየ።

    ረቂቅ ሕጉ ከአሜሪካ፣ እስራኤል እና ቴህራን ጠብ አጫሪ ናቸው ስትል ከምትፈርጃቸው አገራት ጋር ግንኙነት ያላቸው መርከቦችን ማገድ እንደሚያካትት ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ታስኒም የፓርላማ አባል የሆኑትን አባስ ሳሊሚን ጠቅሶ እንደዘገበው የፓርላማው ብሔራዊ ደህንነት እና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኮሚቴ በወሽመጡ እና በፐርዢያ ባሕረ ሰላጤ ላይ አገሪቱ የሚኖራትን ቁጥጥር በሚመለከት ተወያይቷል።

    በረቂቅ ሕጉ መሠረት አሜሪካ፣ እስራኤል እና ኢራን ጠብ አጫሪ ብላ ከፈረጀቻቸው ሌሎች አገራት ጋር ግንኙነት ያላቸውን መርከቦች በወሽመጡ እንዳያልፉ ይከለከላከሉ።

    በረቂቅ ሕጉ በተጨማሪም ከእስራኤል ገር ግንኙነት ያላቸው ወታደራዊ እና የሲቪል የጭነት መርከቦች እንዲሁም በኢራን ላይ በተከፈተው ዘመቻ ድጋፍ ያደረጉ እንዳያልፉ ይከለከላሉ።

    በተጨማሪም በኢራን ላይ ጉዳት በማድረስ ረገድ ኃላፊነት አለባቸው ተብለው የሚታመኑ አገራትና ግለሰቦች፣ ካሳ እስኪከፍሉ ድረስ በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ እና በፋርስ ባሕረ ሰላጤ በኩል የማለፍ ፈቃድ አይሰጣቸውም።

    ረቂቅ ሕጉ ለሚፈጸሙ ጥሰቶች ከባድ ቅጣቶችን፤ ከእነዚህም መካከል በመርከብ ላይ የተጫነው ሸቀጥ ካለው ዋጋ እስከ 20 በመቶ የሚደርስ የገንዘብ ቅጣትን አካትቷል።

    በሕጉ መሠረት፣ መንግሥት በፋርስ ባህረ ሰላጤ ውስጥ የአሰሳ ስራን ለመቆጣጠር፣ የመርከቦችን እንቅስቃሴ ለመከታተል እንዲሁም ደህንነትን እና የአካባቢ ጥበቃን ለማረጋገጥ ከጦር ኃይሎች ጋር በጋራ እንዲሰራ ይጠበቅበታል።

    ሳሊም ሕጉ በባለሙያዎች እየታየ መሆኑን እና ከመጽደቁ በፊት የማሻሻያ ሃሳባቸውን እንዲያቀርቡ ይጠበቃል ብለዋል።

    የኢራን ፓርላማ ረቂቅ ሕጉ ላይ የተወያየው አገሪቱ ከኦማን ጋር በወሽመጡ አስተዳደር ላይ እየተነጋገረች ባለችበት እና ከሥምምነት ይደረሳል ተብሎ በሚጠበቅበት ወቅት ነው።

  15. የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር በፊፋ ፕሬዝዳንት ላይ ዕምነት እደሌለው አሳወቀ

    ጂያኒ ኢንፋንቲኖ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ተቃውሞ የበረታባቸው የፊፋ ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ

    የዓለም ዋንጫ ዝግጅት ድርሻን ለግል ባለሀብቶች አሳልፎ የሚሰጠውን ዕቅዳቸውን ካሳወቁ በኋላ ውዝግብ ውስጥ የገቡት የፊፋ ፕሬዝዳንት ሃሳባቸውን ቢሰርዙም የአውሮፓ የእግር ኳስ ማኅበራት አሁንም ተቃውሞ እያሰሙ ነው።

    አውሮፓውያኑ በፊፋው ፕሬዝዳንት ላይ ዕምነት እንደሌላቸው በመግለጽ እራሳቸውን የዓለም ዋንጫን ጨምሮ በፊፋ ከሚዘጋጁ ውድድሮች እንደሚያገሉ እየዛቱ ነው።

    የአውሮፓ አገራት የእግር ኳስ ማኅበር (ዩኤፋ) ምንም እንኳን የፊፋው ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ የዓለም ዋንጫ ድርሻን የመሸጥ ዕቅድ ቢሰረዝም ያቀረበው ቅድመ ሁኔታ አለመሟላታቸውን በመግለጫው አመልክቷል።

    "የዩኤፋ አባል ማኅበራት በፊፋ በሚዘጋጁ ውድድሮች ላይ ካለመሳተፋቸው ጋር በተያያዘ ያቀረቧቸው ቅድመ ሁኔታዎች ግልጽ ናቸው” ብሏል።

    "የመጀመሪያው የዓለም ዋነኛው የእግር ኳስ ውድድርን ድርሻ የመሸጡ ሃሳብ እንዲቀር፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ እንዲህ ዓይነቱ የዓለም ዋንጫን ገጽታ የሚያበላሽ ማንኛውም ዓይነት ሙከራ በድጋሚ ፈጽሞ እንደማይደረግ ማስተማመኛ ማግኘት ነው” ያለው ማኅበሩ፤ ነገር ግን እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች “አልተሟሉም” ብሏል።

    የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር በፊፋ ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ ላይ እምነት እንደሌለው በመግለጽ የፊፋን አዲስ ዕቅድ ግልጽነት የጎደለውና ደካማ በማለት አጣጥሎታል።

    ዩኤፋ ቅዳሜ ዕለት ባወጣው መግለጫ "በጂያኒ ኢንፋንቲኖ ፕሬዝዳንትነት ላይ እምነት እንደሌለው እና ይህ አቋሙም አልተቀየረም” በማለት በያዘው አቋም መጽናቱን ገልጿል።

  16. ሁቲዎች በየመን መንግሥት ኃይሎች ካምፕ ላይ በፈጸሙት ጥቃት በርካቶችን መግደላቸው ተዘገበ

    ሁቲ ታጣቂዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty

    የሁቲ ታጣቂዎች ዓለም አቀፍ ዕውቅና ባለው የየመን መንግሥት ቁጥጥር ሥር በሚገኝ ካምፕ ላይ ፈጸሙት በተባለ የሮኬት እና የድሮን ጥቃት ቢያንስ 30 ሰዎች መገደላቸው ተዘገበ።

    የየመን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ጥቃቱ የተፈጸመው ማሪብ እና ሃድራማውት በተባሉት ግዛቶች ውስጥ በሚገኙ የታጣቂዎች የመጠለያ ካምፕ ላይ ነው።

    የየመን መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ ኃይሎች ካምፖች ላይ በተፈጸመው ጥቃት በርካታ ሰዎች ከመገደላቸው በተጨማሪ በንብረትም ላይ ከባድ ውድመት መድረሱ ተነግሯል።

    ለዓመታት በሁቲ ኃይሎች እና ዓለም አቀፍ ዕውቅና ባለው የየመን መንግሥት መካከል የእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ ያለችው አገሪቱ በሁለቱ ወገኖች ቁጥጥር ስር ትገኛለች።

    ከአውሮፓውያኑ 2022 ወዲህ በሁለቱ ኃይሎች መካከል የሚደረገው ውጊያ ጋብ ብሎ የቆየ ቢሆንም አልፎ አልፎ ግጭቶች ሲካሄዱ ቆይተዋል።

    ካለፈው ሐምሌ ወር ወዲህ በሁቲዎች እና በየመን መንግሥት መካከል የሚደረገው ግጭት በመባባሱ በሁለቱም ወገን የተሰለፉ በርካታ ተዋጊዎች መገደላቸው ተዘግቧል።

    የኢራን ወዳጅ የሆኑት ሁቲዎች ከአውሮፓውያኑ 2014 ወዲህ ዋና ከተማዋ ሰነዓን እና በቀይ ባሕር ዳርቻ የሚገኙ ሌሎች የአገሪቱን ክፍሎች ተቆጣጥረው ይገኛሉ።

    መቀመጫውን አንደን ያደረገው የየመን መንግሥት የሳዑዲ አረቢያ ድጋፍ ያለው ሲሆን ዓለም አቀፍ ዕውቅናንም አግኝቷል።

    ነገር ግን ሁቲዎች ከየመን መንግሥት በበለጠ በቀጣናው ከፍተኛ ተጽእኖ ያላቸው ሲሆን፣ ከኢራን በሚያገኙት ድጋፍ በቀይ ባሕር ላይ በሚተላለፉ መርከቦች እንዲሁም በሳዑዲ ላይ የሚሳዔል እና የድሮን ጥቃቶችን በመፈጸም ይታወቃሉ።

  17. ዩክሬን በሩሲያ ላይ በፈፀመችው የድሮን ጥቃት ሦስት ሰዎች ሲገደሉ፣ 15 መቁሰላቸው ተገለፀ

    የአደጋ ጊዜ ሠተራኞች በፈራረሰ ቤት ውስጥ

    የፎቶው ባለመብት, State Emergency Service Of Ukraine

    የምስሉ መግለጫ, ሩሲያ እና ዩክሬን አንዳቸው በአንዳቸው ላይ በፈፀሙት ጥቃት ሰላማዊ ሰዎች ተገድለዋል

    ዩክሬን ምሽቱን በሩሲያ የተለያዩ ከተሞች ላይ በፈፀመችው ጥቃት ሦስት ሰዎች ሲገደሉ 15 መቁሰላቸውን ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ጥቃቱ የተፈፀመው በብያንስክ፣ ኒዢኒይ ኖቭጎርድ፣ እና ኩርስክ ከተሞች ውስጥ ሲሆን ከተጎዱት መካከል አንድ ሕፃን ይገኝበታል።

    የብርያንስክ ከተማ ተወካይ አስተዳዳሪ ይጎር ኮቫልቹክ እየተጓዘ ባለ ተሽከርካሪ ላይ በተፈፀመ የድሮን ጥቃት አሽከርካሪው መገደሉን ገልጸዋል።

    ሌላ ግለሰብም በኖቮዝይብኮቭ ከተማ መገደሉ የተዘገበ ሲሆን፣ ሌሎች አምስት ሰዎች ደግሞ ጉዳት ደርሶባቸው ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል።

    በሌላ በኩል የሩሲያ አምስተኛ ትልቅ ከተማ የሆነችው የኒዢኒይ ኖቭጎሮድ አስተዳዳሪ ግሌብ ኒኪቲን፣ ድሮኑ የመገናኛ መስመሩ እክል ከገጠመው በኋላ ዛፍ ላይ በመውደቁ አንድ ሕፃንን ጨምሮ አራት ሰዎች መጎዳታቸውን ገልጸዋል።

    በአቅራቢያው ባለ ቦታ እሳት መነሳቱን የገለፁት ኒኪቲን፣ የደረሰባቸው ጉዳት “ለሕይወታቸው የሚያሳጋ እንዳልሆነ” ተናግረዋል።

    በሩሲያ ኩርስክ ከተማም አንድ ግለሰብ እንደተገደለ የአካባቢው አስተዳዳሪ ተናግረዋል። በዚህ ጥቃት ስድስት ሰዎች ላይ ጉዳት መድረሱን እና የሦስቱ ከባድ ጉዳት መሆኑን አስተዳዳሪው አሌክሳንደር ኪንሽቴን ገልጸዋል።

    የዩክሬን ፕሬዚደንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ ጦሩ በረዥም ርቀት ጥቃት ሁለት የሩሲያ የነዳጅ ማጣሪያን መምታቱን ገልጸዋል።

    "በባሽኮርቶስታን እና ያሮስላቪል የሚገኙ የነዳጅ ማጣሪያዎች ተመትተዋል" ብለዋል ዘሌንስኪ።

    የያሮስላቪል ሰማይም በጥቁር ጭስ ተሸፍኖ ታይቷል።

    የአካባቢው አስተዳዳሪ የተፈፀመውን ጥቃት “በጠላት ድሮኖች የተፈፀመ ሰፊ ጥቃት” ሲሉ የገለፁት ሲሆን 93 ድሮኖች ተመትተው መውደቃቸውን እና በስብርባሪያቸው የነዳጅ ማከማቻ ታንከሮች መመታታቸውን ተናግረዋል።

    የሩሲያ ጦርም በበርካታ አካባቢዎች 605 የዩክሬን ድሮኖችን ማክሸፉን ገልጿል።

    ዩክሬን ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ የሩሲያ መሠረተ ልማት ላይ ተከታታይ ጥቃቶችን እየፈፀመች ሲሆን ሩሲያም ምላሽ እየሰጠች ነው።

    የዩክሬን ባለሥልጣናት በሩሲያ የድሮን ጥቃት ስድስት ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን ገልጸዋል።

  18. ትራምፕ አሜሪካ የተተኳሾች እጥረት እንደገጠማት መረጃ ያወጡት ከባድ እስር ይጠብቃቸዋል ሲሉ ዛቱ

    ተወንጫፊ ተተኳሾችን የሚያንቀሳቅሱ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ከኢራን ጦርነት ጋር በተያያዘ የአሜሪካ የጦር መሳሪያ እና የተተኳሽ ክምችቷ ተመናምኗል መባሉን ፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተባብለው ይህንን በተመለከተ የሐሰት መረጃ የሚያሠራጩት ከባድ እስር ይጠብቃቸዋል ሲሉ ዛቱ።

    ፕሬዝዳንቱ የአሜሪካ የመሳሪያ ክምችት ቀንሷል በሚል የቀረቡ የመገናኛ ብዙኃን ዘገባዎችን አጣጥለው “በተለይ የተወሰኑ ዓይነት ጦር መሳሪያዎች እና ተተኳሾች በከፍተኛ መጠን” እንዳሏቸው ዝርዝር መረጃ ሳይሰጡ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    "በተጨማሪም ከፍተኛ መጠን ያላቸው ተተኳሾች እየተመረቱ እንደ አስፈላጊነታቸው ወደ አሜሪካ ይጓጓዛሉ። የመከላከያ ተቋማት በአሜሪካ ታሪክ ግዙፍ የሆኑ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ፋብሪካዎች እና ማምረቻዎችን እየገነቡ ነው” ብለዋል ትራምፕ።

    የተተኳሾችን እጥረት በተመለከተ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የመከላከያ ሚኒስትሩን ፔት ሄግሴትን ባለፈው አርብ በተካሄደው የካቢኔ ስብሰባቸው ላይ መጠየቃቸውን ዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ ዘግቦ ነበር።

    ጋዜጣው ስማቸው ያልተገለጹ ሁለት ምንጮችን ጠቅሶ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በስብሰባው ላይ ለመከላከያ ሚኒስትሩ የተተኳሾች እጥረቱ “ተፈትቷል” ብለው አስበው እንደነበር እንደነገሯቸው ዘግቧል።

    በዘገባው የተቆጡት ፕሬዝዳንት ትራምፕ “እንዲህ ያለውን በአገር ክህደትነት የሚቆጠር መረጃን አሾልከው የሰጡ ተከስሰው ከፍተኛ የእስር ቅጣት ይጠብቃቸዋል” ሲሉም ዝተዋል።

    የረጅም ርቀት ተወንጫፊ ሚሳዔሎች እና የአየር መከላከያ ሚሳዔሎች እጥረት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ በሚከተሉት ፖሊሲ ላይ ተጽእኖ እንደፈጠረ እና የአሜሪካ ሠራዊት ወደ 80 በመቶ የሚጠጋውን ፀረ ሚሳዔል ክምችቱን ጥቅም ላይ እንዳዋለ ሲኤንኤን ዘግቧል።

    ዋሽንግተን ፖስት በተጨማሪም የተተኳሽ እጥረቱ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ላይ ሊፈጽሙ ሲዝቱበት የነበረውን “በጣም ከባድ” ጥቃት ለመሰረዝ እንዳስገደዳቸው ዘግቧል።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ካሮላይን ሌቬት ፕሬዝዳንቱ እና የመከላከያ ሚኒስትሩ ተጨቃጭቀዋል መባሉን “ሐሰተኛ ዜና” በማለት ይህ እንዳልሆነ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ጽፈዋል።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር - ፔንታገን ቃል አቀባይ ሾን ፓርኔል የጦር መሳሪያ እጥረት መከሰቱን በተመለከተ የቀረቡትን ዘገባዎች “ሙሉ ለሙሉ የፈጠራ” ሲሉ አጣጥለዋቸዋል።

  19. ዩክሬን ሁለት የሩሲያ ነዳጅ ማጣሪያዎች ላይ ጥቃት ፈጸመች

    ጥቃት ደረሰበት ነዳጅ ማጣሪያ

    የፎቶው ባለመብት, Social media

    የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ የአገሪቱ ጦር በፈጸመው ጥቃት በሩሲያ ትልቁ የሆነውን የነዳጅ መሠረተ ልማት ጨምሮ ሁለት ማጣሪያዎች መመታታቸውን ተናገሩ።

    በዚህ ጥቃት የተመቱት በያሮስላቭል ከተማ የሚገኘውን የስላቭኔፍት ያኖስ ማጣሪያ እና በባሽኮርቶስታን ከተማ ያለው ባሽኔፍት ኖቮይል ማጣሪያ መሆናቸውን ፕሬዝዳንቱ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ ገልጸዋል።

    በያሮስላቭል የሚገኘው ነዳጅ ማጣሪያ በዓመት 15 ሚሊዮን በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ የማጣራት አቅም ያለው ግዙፍ መሠረተ ልማት እንደሆነ ተገልጿል። ስፍራው የሚገኘው ከዩክሬን ድንበር 280 ኪሎ ሜትር ርቆ ነው።

    በጥቃቱ በተፈጸመበት ያሮስላቭል ከተማ ከፍተኛ ጭስ ታይቷል።

    የያሮስላቭል ክልል ዋና አስተዳዳሪ “በጠላት ድሮን የተፈጸመ ትልቁ ጥቃት” ሲሉ የገለጹት ሲሆን 93 ድሮኖች እንዲወድሙ መደረጋቸውን ተናግረዋል።

    ይሁን እንጂ ስብርባሪዎች የነዳጅ ማጠራቀሚያን መምታታቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው አስታውቀዋል።

    በከተማው በደረሰው ጥቃት አራት ሰዎች እንደተጎዱም ተገልጿል። የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች እሳቱን ለማጥፋት እየተረባረቡ መሆኑን የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፣ በአሁኑ ሰዓት በአካባቢው ሌላ ስጋት አለመኖሩን ተናግረዋል።

    እንደ የሩሲያ ጦር ገለጻ፤ ዩክሬን ያሮስላቭልን ጨምሮ በመላው አገሪቱ የላከቻቸው 605 ድሮኖች እንዲጠለፉ እና እንዲወድሙ ተደርጓል።

    ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ዩክሬን ነዳጅ ማጣሪያዎች እና መጋዘኖችን ጨምሮ የተለያዩ የሩሲያ መሠረተ ልማቶችን ዒላማ ያደረጉ ጥቃቶችን ስታደርስ ቆይታለች።

  20. እስራኤል ከሳምንታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በደቡባዊ ሊባኖስ ጥቃት ፈጸመች

    ለሊባኖስ ተራራማ ስፍራ ላይ ጭስ ወደላይ ሲወጣ ይታያል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት አንድ ሰው ሲገደል 12 ሰዎች መጎዳታቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር አስታወቀ።

    እስራኤል ይህንን ጥቃት ያደረሰችው በኢራን የሚደገፈው ሄዝቦላህ ፈጽሞታል ላለችው “ግልጽ የተኩስ አቁም ጥሰት” ምላሽ ለመስጠት እንደሆነ ገልጻለች።

    ሞት እና ጉዳት ያጋጠመው በቲብኒን ከተማ ውስጥ የጸሎት ስፍራ ጣርያ በመመታቱ እንደሆነ የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የእስራኤል ጦር ከአንድ ወር በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ነዋሪዎች አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ የሚጠይቅ ትዕዛዝ ባወጣባት በምዕራባዊቷ ማንሱሪ ከተማም ጥቃቶች ተፈጽመዋል።

    የእስራኤል ጦር የአረብኛ ቋንቋ ቃል አቀባይ ረቡዕ ዕለት ነዋሪዎች በአካባቢው “የኃይል እርምጃ” ከመወሰዱ በፊት ለቅቀው እንዲወጡ አዝዘው ነበር።

    ከ30 ደቂቃ በኋላ ደግሞ ዋናው ቃል አቀባይ የእስራኤል ጦር በደቡባዊ ሊባኖስ “ዒላማ ተኮር ጥቃቶችን” ማድረስ መጀመሩን አስታውቀዋል።

    የእስራኤል ጦር ሄዝቦላህ የተኩስ አቁም ስምምነቱን እንደጣሰ ከመግለጽ ውጪ ዝርዝር መረጃ አላቀረበም።

    እነዚህ ጥቃቶች የተፈጸሙት የእስራኤል እና ሊባኖስ ባለሥልጣናት በአሜሪካ አደራዳሪነት የተደረሰውን ተኩስ አቁም ለማጽናት ያለመ ንግግር ሮም ውስጥ እያካሄዱ ባለበት ወቅት ነው። ሄዝቦላህ ክስተቶቹን በተመለከተ አስተያየት አልሰጠም።

    ሁለቱ አገራት፣ ሄዝቦላህ ትጥቁን እንዲፈታ፣ በምላሹ ደግሞ እስራኤል ወርራ ከያያዘቻቸው የደቡባዊ ሊባኖስ ግዛቶች እንድትወጣ የሚያደርግ የስምምነት ማዕቀፍ ሰኔ ላይ ተፈራርመው ነበር።

    የእስራኤል መውጣት ከትጥቅ መፍታት ጋር መያያዙ “ሁሉምን ቀይ መስመሮች” የጣሰ እንደሆነ የገለጸው ሄዝቦላህ፣ ስምምነቱን ውድቅ አድርጎታል።