ትራምፕ ዛሬ ስምምነት ይፈረማል ብለው ሲጠብቁ፤ ኢራን በቀጣይ ቀናትም ሊሆን እንደሚችል ጠቁማለች

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ እሑድ ከኢራን ጋር ስምምነት ይፈረማል ብለው እየጠበቁ ነው። የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ግን ስምምነቱ ዛሬ እንደማይፈረም እና በቀጣይ ቀናት ሊፈረም የሚችልበት ዕድል እንዳለ መናገራቸው ተዘግቧል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ ዛሬ ስምምነት ይፈረማል ብለው ሲጠብቁ፤ ኢራን በቀጣይ ቀናትም ሊሆን እንደሚችል ጠቁማለች

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Bloomberg via Getty Images

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ እሑድ ከኢራን ጋር ስምምነት ይፈረማል ብለው እየጠበቁ ነው። የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ግን ስምምነቱ ዛሬ እንደማይፈረም እና በቀጣይ ቀናት ሊፈረም የሚችልበት ዕድል እንዳለ መናገራቸው ተዘግቧል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት ቃል አቀባዩ ከአሜሪካ ጋር የተደረሰው “የመጨረሻ ስምምነት ሳይሆን ውዝግብ የሚያስነሱ ጉዳዮችን በተመለከተ አጠቃላይ አቅጣጫ ማስቀመጥ ነው” ብለዋል።

    ስምምነቱ ዛሬ እሑድ ባይፈረምም እንኳን በቀጣይ ቀናት የመፈረም ዕድል እንዳለ አክለዋል።

    የፓኪስታንጠቅላይ ሚኒስትር ሻሀባዝ ሻሪፍ ሁለቱ ወገኖች የመግባቢያ ሰነዱ ላይ እንደተስማሙ ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንትዶናልድ ትራምፕም በ80ኛ ዓመት ልደታቸው ቀን ስምምነቱ እንደሚፈረም እየጠበቁ ነው።

    ሁለቱን አገራት በዋናነት ያሸማገሉት ፓኪስታን እና ኳታርን ጨምሮ ሌሎች አገራትም ስምምነቱ ላይ ኤሌክትሮኒክ ፊርማቸውን ያኖራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    በመግባቢያ ሰነዱ መሠረት የተኩስ አቁሙ ለ60 ቀናት ተራዝሞ ስለ ኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ድርድር ይጀመራል ተብሏል።

    ከአሸማጋዮቹአንዷ የሆነችው የኳታር ልዑካን ቴህራን የገቡ ሲሆን፤ ልዑካኑ በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የመልዕክት ልውውጥን እያሳለጡ መሆኑም ተገልጿል።

    ትራምፕ ስምምነቱ እንደተፈረመ በአፋጣኝ የሆርሙዝ ወሽመጥ ይከፈታል ብለዋል።

  2. አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለው ሶማሊያዊ አሠልጣኝ ሙሉ ክፍያ እንደሚሰጠው ፊፋ ገለጸ

    ኦማር አርታን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለው ሶማሊያዊ አሠልጣኝ ኦማር አርታን ሙሉ ክፍያ እንደሚሰጠው ፊፋ ገለጸ።

    የዓለም ዋንጫን ይዳኛል ተብሎ የነበረው አሠልጣኝ ግጥሚያዎችን መዳኘት ባይችልም እንኳን ሙሉ ክፍያው እንደሚሰጠው ፊፋ አስታውቋል።

    ኦማር አርታን በማያሚ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ለ11 ሰዓት መጠይቅ ከተደረገለት በኋላ ወደ አሜሪካ እንዳይገባ ተከልክሏል።

    የዲፕሎማት ፓስፖርቱ እና አንድ ጊዜ አሜሪካ እንዲገባ የሚፈቅደው ቪዛው ተቀባይነት አላገኙም።

    የአሜሪካ ባለሥልጣን እንዳሉት አሠልጣኙ “በሽብርተኛነት ከተጠረጠሩ ቡድኖች ጋር ትስስር እንዳለው ስለሚታመን” ክልከላ ተጥሎበታል።

    አሠልጣኙ ከአሜሪካ የኢምግሬሽን ባለሥልጣኖች ከአል-ሻባብ ጋር ግንኙነት እንዳለው ተጠይቆ ምንም ትስስር እንደሌለው መግለጹን ተናግሯል።

    “ሕጋዊ ሰነዶች ይዤ ነበር። ትክክለኛ ቪዛ ነበረኝ። ሕልሜን ለመኖር የምሞክር አሠልጣኝ ነኝ። ትልቁ ሕልሜ የዓለም ዋንጫን መዳኘት ነበር” ብሏል።

    ወደ ቱርክ የሚጓዝ አውሮፕላን ውስጥ እንዲገባ ከተደረገ በኋላ ወደ ሶማሊያ እንዲመለስ ፊፋ እገዛ ማድረጉ ተገልጿል።

    ሞቃዲሹ ሲገባም ደማቅ አቀባበል ተደርጎለታል።

  3. ኢራን ስምምነቱን በተመለከተ የመጨረሻ ውሳኔ ላይ እንዳልደረሰች ተገለጸ

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር ዛሬ ይፈረማል ተብሎ የሚጠበቀውን የመግባቢያ ሰነድ በተመለከተ የመጨረሻ ውሳኔ ላይ እንዳልደረሰች ለድርድሩ ቅርበት ያላቸውን ምንጮች ጠቅሶ የፋርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    ኢራን “የቀረበው ምክረ ሐሳብ ፖለቲካዊ፣ ሕጋዊ እና ቴክኒካዊ ይዘቶችን መመልከታችንን ቀጥለናል” ማለቷን ዘገባው አትቷል።

    ለቴህራን ወታደራዊ እና የደኅንነት ተቋማት ቅርብ የሆነው የፋርስ የዜና ወኪል “የሚመለከታቸው ተቋማት ምክረ ሐሳቡን አሁንም እየተመለከቱት ነው” ብሏል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ ስምምነቱ ይፈረማል ብለው እየጠበቁ ሲሆን፤ ከአሸማጋዮቹ አንዷ የሆነችው የኳታር ልዑካን ዛሬ ቴህራን ገብተዋል። ልዑካኑ በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የመልዕክት ልውውጥን እያሳለጡ መሆኑም ተገልጿል።

  4. ዩኬ ማዕቀብ የተጣለበት ነዳጅ የጫነ የሩሲያ መርከብ መያዟን አስታወቀች

    ማዕቀብ የተጣለበት ነዳጅ የጫነ የሩሲያ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የዩናይትድ ኪንግደም ወታደሮች ማዕቀብ የተጣለበት ነዳጅ የጫነ የሩሲያ መርከብን በኢንግሊሽ ካናል ላይ መያዛቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር አስታወቁ።

    ‘ስማይትሮስ’ የተባለውን መርከብ በቁጥጥር ሥር ለማዋል የአገሪቱ የባሕር ኃይል እና ልዩ ሥልጠና የተሰጠው ብሔራዊ የወንጀል ቁጥጥር ኤጀንሲ ተጣምረው ስድስት ሰዓታት የፈጀ ኦፕሬሽን ማካሄዳቸው ተገልጿል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመር “ይህ ስኬታማ ኦፕሬሽን ሩሲያን የሚያዳክም እና ፑቲን በዩክሬን የከፈተው ጦርነት መደበቂያ እንደማይሆነው የሚያሳይ ነው” ብለዋል።

    ሩሲያ የተጣለባትን ዓለም አቀፍ የነዳጅ ማዕቀብ ለማለፍ በምሥጢራዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ድብቅ መርከቦችን (shadow fleet) ታሰማራለች።

    ወደ 700 የሚጠጉት እነዚህ መርከቦች ማዕቀብ የተጣለበት 75% የሚሆነውን የሩሲያ ነዳጅ በማዘዋዋር የክሬምሊን የጀርባ አጥንት ሆነው ያገለግላሉ።

    ዩኬ ከ500 በላይ በሚሆኑ መርኮች ላይ ማዕቀብ መጣሏን አስታውቃለች።

  5. ሰሜን ኮሪያ የኒውክሌር መሣሪያን በተመለከተ አቋሟን እንደማትለውጥ ገለጸች

    የፒዮንግያንግ የኒውክሌር መሣሪያ ግንባታ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    ሰሜን ኮሪያ ኒውክሌርን በተመለከተ ያላት አቋም “እንደማይቀለበስ” በመግለጽ የኒውክሌር መሣሪያ ግንባታዋን እንድታቆም የቀረበላትን ጥያቄ ውድቅ አደረገች።

    የደቡብ ኮሪያ፣ ጃፓን እና አሜሪካ ባለሥልጣናት ባደረጉት ውይይት የኮሪያ ቀጣና ከኒውክሌር መሣሪያ ነጻ እንዲሆን ቁርጠኛ መሆናቸውን ቢገልጹም ፒዮንግያንግ ሐሳቡን አልተቀበለችም።

    የቀረበላት ጥያቄ “ምክንያት አልባ” እና “የሕልም ዓለም” እንደሆነ በመግለጽ ምላሽ ሰጥታለች።

    የኒውክሌር መርሃ ግብሯን የምትቀጥልበት ምክንያት አሜሪካ የኒውክሌር መሣሪያ ሥርዓት ለደቡብ ኮሪያ እና ጃፓን ማቅረቧ እንደሆነ ሰሜን ኮርያ አስረግጣ ተናግራለች።

    በአውሮፓውያኑ 2019 ከዋሽንግተን ጋር ያደረጉት ውይይት መክሸፉን ተከትሎ ፒዮንግያንግ የኒውክሌር መሣሪያ ግንባታዋን አጠናክራ ገፍታበታለች።

  6. ኢራን ጥርጣሬ ቢገባትም ትራምፕ ዛሬ ስምምነት ይፈረማል ብለው እየጠበቁ ነው

    ኢራን

    የፎቶው ባለመብት, Atta Kenare / AFP via Getty Images

    አሜሪካ እና ኢራን ለረዥም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረውን ስምምነት ዛሬ ይፈራረማሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የፓኪስታን ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ በ80ኛ ዓመት ልደታቸው ቀን ስምምነቱ እንደሚፈረም እየጠበቁ ነው።

    ሆኖም ኢራን ስምምነቱ የሚፈረምበት ጊዜ ላይ አሁንም ጥርጣሬ እንዳላት ገልጻለች። የስምምነቱን መፈረም በተመለከተ ኢራናውያን ተቃዋሚዎችም ቅሬታ አሰምተዋል።

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሻሀባዝ ሻሪፍ በበኩላቸው ሁለቱ ወገኖች የመግባቢያ ሰነዱ ላይ እንደተስማሙ ገልጸዋል። ኢስላማባድ ስምምነቱ ላይ ኤሌክትሮኒክ ፊርማዋን እንደምታኖርም አክለዋል።

    ስምምነቱ ከተፈረመ በኋላ በቀጣይ ሳምንት የባለሙያዎች ውይይት እንደሚቀጥል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    ትራምፕ ስምምነቱ እንደተፈረመ በአፋጣኝ የሆርሙዝ ወሽመጥ ይከፈታል ብለዋል።

    ሁለቱን አገራት በዋናነት ያሸማገሉት ፓኪስታን እና ኳታርን ጨምሮ ሌሎች አገራትም ስምምነቱ ላይ ይፈርማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    በመግባቢያ ሰነዱ መሠረት የተኩስ አቁሙ ለ60 ቀናት ተራዝሞ ስለ ኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ድርድር ይጀመራል ተብሏል።

  7. አሜሪካ እና ኢራን የመጀመሪያ ደረጃ ስምምነት በ24 ሰዓት ውስጥ እንደሚፈራረሙ ፓኪስታን አስታወቀች

    ቴህራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዩናይትድ ስቴትስ እና ኢራን በሰላም ድርድሩ ማዕቀፎች ላይ መስማማታቸውን እና የመጀመርያ ደረጃ ስምምነቱን በ24 ሰዓታት ውስጥ እንደሚፈራረሙ ፓኪስታን አስታወቀች።

    የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሻህባዝ ሻሪፍ ቅዳሜ ዕለት እንዳሉት ከሆነ ከሦስት ወር በላይ የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆም የሚያስችለው የመጀመሪያ ደረጃ የሰላም ስምምነት በሚቀጥሉት 24 ሰዓት ውስጥ ይፈረማል።

    የአደራዳሪዋ ፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሻሪፍ የፊርማ ስነ ስርዓቱ በኤሌክትሮኒክስ እንደሚሆን እና በሚቀጥለው ሳምንት የሁለቱ አገራት ባለሥልጣናት ዝርዝር ጉዳዮች ላይ ውይይት እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን አርብ ዕለት ለስምምነት መቃረባቸውን የተናገሩ ሲሆን የዩኤስ ባለሥልጣናት ሁለቱም በጽሑፍ ደረጃ መግባባታቸውን እና ዋሺንግተን የመጀመርያ ደረጃ ስምምነቱን በሚቀጥሉት ቀናት እንደምትፈርም ተናግረው ነበር።

    ሻሪፍ በኤክስ ገጻቸው ላይ “ከምን ጊዜውም በበለጠ ወደ ሰላም ስምምነት ተቃርበናል። በሚቀጥሉት 24 ሰዓታት ውስጥ የቀሩ ነገሮችን እናጠናቅቃለን፤ ፓኪስታን ከዚያ ቀጥሎ ወዲያውኑ በኤሌክትሮኒክስ እንዲፈረም ታደርጋለች፤ በሚቀጥለው ሳምንትን በቴክኒክ ደረጃ ውይይቱ ይቀጥላል” ሲሉ ጽፈዋል።

    “ይህ ታሪካዊ የሰላም ስምምነት ዘላቂ ለሆነ ሰላም መሠረት እንደሚጥል እንተማመናለን።”

    የኢራን ጦርነት የተቀሰቀሰው የካቲት 21 2018 ዓ.ም. እስራኤል እና ኢራን በጥምረት ቴህራን ላይ ድብደባ ከፈጸሙ በኋላ ነው።

    በምላሹም ኢራን በባሕረ ሰላጤው በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮች ላይ ድብደባ ፈጽማለች። የሄዝቦላህ ታጣቂዎችም አጋርነታቸውን ለማሳየት ወደ ኢራን ሮኬቶችን አስወንጭፈዋል።

  8. ኢራን የቀድሞውን ጠቅላይ መሪ ለመቅበር የስድስት ቀን የቀብር መርሃ ግብር ይፋ አደረገች

    በእስራኤል እና አሜሪካ ጥቃት የተገደሉት ኢራን ተቅላይ መሪን ምሥል እና የኢራን ሰንደቅ ዓላማን የያዘ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, AP

    ቴህራን ለቀድሞውን ጠቅላይ መሪ አሊ ኻሚኔ የቀብር እና የሀዘን ስነ ስርዓት የስድስት ቀን መርሃ ግብር ማውጣቷን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    አያቶላህ አሊ ኻሚኔ አሜሪካ እና እስራኤል በፈፀሙት ጥቃት መገደላቸው ይታወሳል። ግድያቸው ለሦስት አስርት ዓመታት በእስላማዊ ሪፐብሊክ አገር ላይ የነበራቸውን መሪነት እንዲያከትም አድርጓል።

    የቀብር ሥነ ስርዓቱ ከሰኔ 27 እስከ 28 የሚጀመር ሲሆን ግብዓተ መሬታቸው ደግሞ ሐምሌ 2/2018 ዓ.ም. በኢማም ሬዛ ቅዱስ ስፍራ እንደሚፈፀም ተገልጿል።

    ቀብራቸው 'አሹራ' በመባል በሚታወቀው በእስላማዊ የዘመን መቁጠሪያ የመጀመሪያ ወር እና የነብዩ መሐመድ የልጅ ልጅ ኢማም ሁሴን ቢን አሊ በሞቱበት ቀን በመሆኑ ቁልፍ እንደሆነ ተነግሯል።

    በቀብር መርሃ ግብሩ 20 ሚሊዮን ሰዎችን ለማስተናገድ መታቀዱን የቴህራን ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

  9. የዩኬ መንግሥት ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ ከሩሲያ ነዳጅ ማስገባት ሊያቆም ነው

    አውሮፕላን ነዳጅ እየቀዳ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት የናፍጣ ዘይት እና የአውሮፕላን ነዳጅ ከፈረንጆቹ ጥር 1 2027 ጀምሮ ከሩሲያ ማስገባት ሊያቆም ነው።

    እስከ ጥር 2027 ድረስ ቀን የተቆረጠለት የነዳጅ እግዱ በዩክሬን ጦርነት ምክንያት የዩናይትድ ኪንግደም በሞስኮ ላይ የጣለችው ማዕቀብ አካል ነው።

    የዩኬ መንግሥት ባለፈው ግንቦት አዲስ ማዕቀቦችን ማስተዋወቁን ተከትሎ በሦስተኛ አገር የተጣራውን የአውሮፕላን ነዳጅን ጨምሮ የሞስኮ ነዳጅ ዘይት ቀስ በቀስ ለማቆም እንዳሰበ ተናግሯል። በዓለም አቀፍ የነዳጅ አቅርቦት ችግር ምክንያት ቀስ በቀስ ለማቆም ማሰቡን ገልጿል።

    ይህ እርምጃ ተቃውሞ የተከለው ሲሆን፤ የአውሮፓ ኅብረት “በሞስኮ ላይ ማዕቀቦችን ለመጨመር ጊዜ አይደለም” ብሏል።

    የንግድ ሚኒስትር ክሪስ ብራያንት “ይህ የመጨረሻ ቀን በሩሲያ ላይ ከፍተኛ ግፊትን እንደምንቀጥል ግልፅ ምልክት ነው” ብለዋል።

    የአገሪቱ መንግሥት ምርቶቹን ለመላክ የተሰጠው ጊዜያዊ ፍቃድ በየሁለት ሳምንቱ ይገምገማል ብሏል። ይህ የግምገማ ሂደት ፍቃዱ እ.አ.አ ከጥር 1 ቀን በፊት ሊሰረዝ እንደሚችል ይጠቁማል።

    ብራያንት “ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጊዜያዊ አጠቃላይ ፍቃዱን ለነዳጅ እና ለአውሮፕላን ነዳጅ በየሁለት ሳምንቱ እንደምንገምግም እና ተገቢ ሲሆን ለማንሳት ቃል ገብቻለሁ” ብለዋል።

  10. ኢራን እና አሜሪካ ስምምነት ለመፈራረም በተቃረቡበት ወቅት እስራኤል በሊባኖስ ላይ የአየር ድብደባ ፈጸመች

    ቅዳሜ ዕለት በደቡብ ሊባኖስ ድብደባ ከተፈጸመ በኋላ ጭስ አካባቢውን ሸፍኖታል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ 20 የተለያዩ ስፍራዎች ጥቃት መፈጸሟን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    እስራኤል ጥቃቱን ከመፈጸሟ በፊት ነዋሪዎች አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ ሰጥታ ነበር።

    በታየር አውራጃ ማራኬህ ከተማ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ አንድ ሰው መሞቱን የሊባኖስ ብሔራዊ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የእስራኤል ጦር ድብደባውን የፈጸመው የኢራኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከአሜሪካ ያደረጉት ድርድር ከስምምነት ላይ ሊደረስ መቃረቡን ከተናገሩ በኋላ ነው።

    ስምምነቱ ከሦስት ወር በላይ የቆየውን ጦርነት ከማስቆም ባሻገር የሆርሙዝ ወሽመጥን ያስከፍታል ብለዋል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ ስምምነቱ በእስራኤል እና በሄዝቦላህ መካከል የሚካሄደውን ግጭት ያስቆማል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረው ነበር።

    ከዚህ ቀደም የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ሄዝቦላህ ወደ ሰሜን እስራኤል ሮኬቶችን እና ድሮኖች ማስወንጨፉን ከቀጠለ ድብዳባ እንደሚያካሄዱ ዝተው ነበር።

  11. ዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ ለኢራን በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር ልትሰጥ ነው-ምንጮች

    ቴህራን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ዩናይትድ አረብ ኤሚሬትስ (ዩኤኢ) በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላሮች ለኢራን ለመስጠት መስማማቷን አራት ምንጮች ለሮይተርስ ተናገሩ።

    ኢራን በተከታታይ ሳምንታት ዩኤኢ ላይ ጥቃት ከፈጸመች በኋላ እርምጃው የፖሊሲ ለውጥ ነው ሲሉ ገልጸውታል።

    የዩኤኢ ውሳኔ የተሰማው ቴህራን እና ዋሺንግተን ጦርነቱን ለማስቆም እያደረጉት ያለው ድርድር ላይ ከመግባባት መደረሳቸው ከተገለጸ በኋላ ነው።

    ለንግግሩ ቅርበት ያላቸው ዲፕሎማቶች ዩኤኢ ለኢራን የምትሰጠው በአስር ቢሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር የአሜሪካን ማዕቀብ ተከትሎ በተለያዩ የውጭ አገር ባንኮች እንዳይንቀሳቀሱ የተደረጉ ከነዳጅ ዘይት ሽያጭ ያገኘቻቸውን ገቢ ያካትታል ብለዋል።

    ሁለት የቀጣናው ምንጮች ለሮይተርስ እንደተናገሩት ዩኤኢ 10 ቢሊዮን ዶላር ለመስጠት የተስማማች ሲሆን ከ3 ቢሊየን በላይ የሚሆነው አስቀድማ አስተላልፋላታለች።

    ሁለት ጉዳዩን የሚያውቁ ምንጮች ደግሞ ዩኤኢ የምትሰጠው ገንዘብ በአጠቃላይ 20 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ ይናገራሉ።

    ስምምነቱ ኢራን ዩኤኢ ላይ ጥቃት ላለመፈጸም መስማማቷን ተከትሎ የተደረሰ መሆኑን ጨምረው አስታውቀዋል።

    አንድ የመረጃ ምንጭ በበኩላቸው ለቴህራን 3 ቢሊዮን ዶላር በመጀመርያ ዙር ተሰጥቷታል ብለዋል።

    ሮይተርስ ገንዘቡ የዩኤኢ ይሁን ወይም በዩኤኢ ባንኮች የተቀመጠ እና እንዳይንቀሳቀስ እገዳ የተጣለበት ማረጋገጥ አልቻለም።

    የዩኤኢ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዘገባውን ውድቅ አድርገው 3 ቢሊዮን ዶላር ሰጥታለች የሚለውን መረጃ ሙሉ በሙሉ አጣጥለውታል።

    “እነዚህ ክሶች ሙሉ በሙሉ ሐሰት እና መሠረተ ቢስ መሆናቸውን ማረጋገጥ እንፈልጋለን። የታገደ የኢራን ገንዘብ በተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ በኩል አልተለቀቀም። አልተላለፈም ወይም አልተመቻቸም።”

    የዩኤኢ መግለጫ ተጨማሪ ያለው ነገር የለም።

    ከዚህ ቀደም ሮይተርስ ስለ ገንዘብ ዝውውሩ የዩኤኢ ባለሥልጣናትን ሲጠይቅ አገራቸው ውጥረትን ለማርገብ እና ሰላም ለማምጣት እየሰራች መሆኑን ተናግረው ነበር።

  12. የአሜሪካ ጦር የኢራንን ድሮን መትቶ መጣሉን ምንጮች ለሮይተርስ ተናገሩ

    የአሜሪካ ጦር አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ ጦር በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ እየበረሩ የነበሩ የኢራን አጥፍቶ ጠፊ ድሮኖችን መትቶ መጣሉን ምንጮች ለሮይተርስ ዜና ወኪል ተናገሩ።

    ዋሺንግተን እና ቴህራን በሰላም ስምምነቱ ዙሪያ መግባባት ላይ ደርሰው ፊርማቸውን ያስቀምጣሉ ተብሎ በሚጠበቅበት በአሁኑ ወቅት ግጭቶች መቀጠላቸውን እንደሚያሳይ እኚሁ ምንጭ ለሮይተርስ ተናግረዋል።

    ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁት እኚህ ምንጭ ሰው አልባ አውሮፕላኖች የንግድ መርከብ እንቅስቃሴ ላይ አደጋ ደቅነዋል ብለዋል።

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አርብ ዕለት ቴህራን ድሮኖችን ማሰወንጨፏን እና ሆርሙዝን ለማቋረጥ የሚሞክሩ መርከቦች ላይ አደጋ መጣል እንድታቆም በማስጠንቀቅ “ሁኔታዎችን ወደ መቆጣጠር መምጣት አለባቸው፤ በፍጥነት” ብለዋል።

  13. ኢራን ጦርነቱን ለማስቆም የሚደረገው ስምምነት ሆርሙዝን ዳግም ለመክፈት ያስችላል አለች

    በሚያዚያ ወር የተኩስ አቁም ላይ ከተደረሰ በኋላ በቴህራን ሕይወት ወደ መደበኛ መልኩ የተመለሰ ይመስላል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በሚያዚያ ወር የተኩስ አቁም ላይ ከተደረሰ በኋላ በቴህራን ሕይወት ወደ መደበኛ መልኩ የተመለሰ ይመስላል

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከአሜሪካ ጋር ጦርነቱን ለማስቆም የሚደረገው ድርድር ላይ ከስምምነት ለመድረስ መቃረባቸውን እና ሆርሙዝምን ዳግም ለማስከፈት የሚያስችል መሆኑን ተናገሩ።

    ሰይድ አባስ አራጋቺ ለአገር ውስጥ ቴሌቪዥን እንደተናገሩት ስምምነቱ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ እንቅስቃሴ ላይ የተጣለው እገዳም እንዲነሳ ያደርጋል።

    ነገር ግን በኢራን የኒውክሌር ፕሮግራም ላይ የሚደረገው ድርድር ከዚህ በኋላ እንደሚጀመር አስታውቀዋል።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት የስምምነቱ የተወሰኑ ዝርዝሮችን እውነተኛ መሆናቸውን አረጋግጠው የኢራን ምጣኔ ኃብታዊ ተጠቃሚነት ቴህራን ግዴታዎቿን በማክበሯ ላይ የተመሠረቱ ናቸው ብለዋል።

    የኢራን ጦርነት የተጀመረው የካቲት 21 2018 ዓ.ም. እስራኤል እና አሜሪካ ድብደባ ከፈጸሙ በኋላ ነው።

    ከዚያ በኋላ የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ ዘይት እና የተፈጥሮ ጋዝ መተላለፊያ የሆነው የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ በሙሉ ተዘግቷል።

    በሚያዚያ ወር በሁለቱ አገራት መካከል የተኩስ አቁም ቢደረስም ኢራን እና አሜሪካ ይህንን ሳምንት ጨምሮ አንዳቸው ሌላኛቸው ላይ ድብደባ ፈጽመዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ሐሙስ ዕለት ኢራን ላይ ለመፈጸም “ታቅዶ የነበረውን ጥቃት” መሰረዛቸውን ተናግረዋል።

    ፕሬዚዳንቱ ለምን እነደሰረዙት ሲያስረዱም ተደራዳሪዎች ሊፈረም የሚችል “ስምምነት ላይ ደርሰዋል” ብለዋል።

    አርብ ዕለት የኢራን ብዙኃን መገናኛዎች ሁለቱ አገራት የሚደራደሩባቸውን ባለ 14 ነጥብ ሰነድ ውስጥ የተወሰነውን አጋርተዋል።

    ትራምፕ ግን “ከተስማማንባቸው ነጥቦች ጋር ምንም ግንኙነት የላቸውም” እንዲሁም “ከእውነታው ጋር ምንም ትስስር የለውም” ሲሉ ውድቅ አድርገውታል።

    ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ደግሞ የአደራዳሪዋ ፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስት ሼህባዝ ሻሪፍ ሁለቱ አገራት እየተነጋገሩበት ያለው የመግባቢያ ሰነድ ላይ ከስምምነት ተደርሷል የመጨረሻ ጉዳዮች ብቻ እየተጠበቁ ናቸው ብለዋል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራጋቺ በጠቅላይ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ውስጥ የአዲሱ ስምምነት “ደጋፊዎች እና ነቃፊዎች” መኖራቸውን እንደገለጹ የአገሪቱ ብዙኃን መገናኛዎች ዘግበዋል።

    ይሁን እንጂ የጋራ ውሳኔ ላይ አልደረሰንም ካሉ በኋላ “ለአሁኑ መጠበቅ ይኖርብናል። ስምምነቱ ከጸደቀ ከርቀት ይፈረማል” ሲሉ አክለዋል።

    እስራኤል በአሜሪካ እና ኢራን ስምምነት ውስጥ ተሳታፊ አይደለችም። ለዓመታት ኢራን በምዕራባዊያን የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ልትገነባ ነው የሚል ውንጀላ ሲቀርብባት ቆይቷል።

    ኢራን በበኩሏ ፕሮግራሙ ለኤሌትሪክ ኃይል እና ለምርምር አገልግሎት ብቻ የሚውል ነው በማለት ስታስተባብል ነበር።

  14. የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ታጣቂዎች “እጃቸውን እንዲሰጡ” አስጠነቀቁ

    የናይጄሪያው ፕሬዝዳንት ቦላ ቲኑቡ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የናይጄሪያው ፕሬዝዳንት ቦላ ቲኑቡ

    በናይጄሪያ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ቡድኖች “እጃቸውን እንዲሰጡ ካልሆነ ግን አገሪቷ ባላት ኃይል ሁሉ እንደሚመቱ” ፕሬዝዳንት ቦላ አሕመድ ቲኑቡ አስጠነቀቁ።

    ፕሬዝዳንቱ ይህን ያሉት አገራቸው እአአ በ1999 ወደ ሲቪል አስተዳደር የተመለሰችበትን ‘የዲሞክራሲ ቀን’ በማስመልከት በብሔራዊ መገኛኛ ብዙኃን ባስተላለፉት መልዕክት ነው።

    በመልዕክታቸው በቅርቡ የተፈፀመው የተማሪዎች እገታ የዚህ ዓመቱን በዓል እንዳደበዘዘው ተናግረዋል።

    ሆኖም የአገሪቷ ፀጥታ ጉዳይ ከመንግሥት እጅ አለመውጣቱን ገልጸዋል።

    "ዲሞክራሲ ያለ ደኅንነት ተጨባጭ አይደለም” ያሉት ፕሬዝዳንቱ፣ ከ50 ሺህ በላይ አዳዲስ የፖሊስ መኮንኖችን፣ ለመከላከያ እና ለፀጥታ 4 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ በጀት መመደባቸውን አስታውቀዋል።

    በሺዎች የሚቆጠሩ አዲስ ወታደራዊ ምልመላዎችም እንዲካሄዱ ተወስኗል ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ከሦስት ዓመት በፊት ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ጦራቸው ባለፈው ዓመት ብቻ 13 ሺህ "ሽብርተኞችን" መግደሉን እና በታጣቂዎቹ ምክንያት የሚደርስ የንጹኃን ሞትም ከአውሮፓውያኑ 2015 ወዲህ በ81 በመቶ መቀነሱን ተናግረዋል።

    ከ124 ሺህ በላይ ተዋጊዎች እና ቤተሰቦቻቸው መሣሪያቸውን ማውረዳቸውንም አክለዋል።

    ሆኖም ተንታኞች በታጣቂዎች የሚፈፀሙ ጥቃቶች በተለያዩ ግዛቶች ነዋሪዎች ላይ ተፅዕኖ ማሳደር መቀጠላቸውንና ወደ ደቡባዊ የአገሪቱ ክፍሎችም እየተዛመቱ መሆናቸውን ገልጸዋል።

  15. ከኢራን ጋር ግንኙነት ያለው ቡድን የአሜሪካ ደኅንነት ተቋማትን የድሮን መረጃ መጥለፉን አስታወቀ

    ፊቱ የማይታይ የበይነ መረብ መረጃ መዝባሪ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በበይነ መረብ ላይ የጽንፈኛ ቡድኖችን እንቅስቃሴ የሚከታተለው ድርጅት ከኢራን ጋር ግንኙነት ያለው የበይነ መረብ ሰርሳሪ ቡድን የአሜሪካ ደኅንነት ተቋማት የሆኑትን ሲአይኤን እና ኤፍቢአይ የድሮኖች ሥርዓትን ሰብሮ በመግባት የዓለም ዋንጫን ዒላማ ማድረጉን መግለጹን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ተቋም የሆነው "ሰርች ቱ አይደንቲፋይ ኢንተርናሽናል ቴረሪስት ግሩፕስ” ባወጣው መግለጫ “ሃንዛላህ” የተባለው ቡድን “በድሮን ለወራት የተቀረጹ ምሥሎች እና መረጃዎችን ማግኘት መቻሉን” አሳውቋል ብሏል።

    የመረጃ መረብ ቀበኞቹ (ሃከርስ) ድሮኖቹ በፀረ ሽብር ዘመቻዎች ወቅት የሰዎችን ገጽታ እና የመኪኖችን የሰሌዳ ቁጥር የሚለይ ቴክኖሎጂ ያላቸው መሆኑን አስታውቀዋል።

    የአሜሪካ ፌደራል መንግሥት ፖሊሶችን እና የኤፍቢአይ ወኪሎችን የዓለም ዋንጫ ውድድሮች በሚካሄድባቸው ስታዲየሞች ዙሪያ በማሰማራት ጥበቃ እያደረገ ሲሆን ፈቃድ ያላገኙ ድሮኖች እንዳይንቀሳቀሱ ተከልክለዋል።

    የአሜሪካ ፍትሕ ሚኒስቴር ቀደም ሲል ከኢራን ጋር ግንኙነት ባላቸው ወገኖች የበይነ መረብ ጥቃት ሊፈጸም የሚችልበት አጋጣሚ ሊኖር እንደሚችል አስጠንቅቆ ነበር።

    ሃንዛል የተባለው ቡድን ከድሮኖች የተመዘበሩ ናቸው ያላቸውን ምሥሎች እና ቪዲዮዎችን ይፋ ደያረገ ሲሆን፣ የአሜሪካ የደኅንነት መሥሪያ ቤቶች ግን ድሮኖቹ ሃክ በመደረጋቸው (በመጠለፋቸው) ላይ ጥያቄ አንስተዋል።

    የሽብር ቡድኖችን የሚከታተለው ድርጅት እንዳለው ይፋ ከሆኑት ቪዲዮዎች መካከል አንዱ ጠለፋው የተፈጸመው በታኅሣሥ 2024 ፖሊስ የአንድ ተቋምን ሶፍት ዌር በተጠቀመበት አጋጣሚ መሆኑን አመልክቷል።

    የመረጃ መዝባሪው ቡድን ሃንዛል በበኩሉ ባለፈው መጋቢት ወር የኤፍቢአይ ዳይሬክተር የሆኑትን ካሽ ፓቴልን የግል አካውንት በመስበር የግለሰቡን ግላዊ ፎቶዎችን እና ሌሎች መረጃዎችን አጋርቷል።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የዚህን የመረጃ ቀበኛ ቡድን አባላትን ለሚጠቁሙ ሰዎች እስከ 20 ሚሊዮን ዶላር ድረስ ሽልማት ለመስጠት ቃል ገብቷል።

  16. ከአሜሪካ ጋር የተደረሰው ስምምነት በኢራን ባለሥልጣናት እስኪጸድቅ እየተጠበቀ መሆኑ ተዘገበ

    የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ እና የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images/Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ቫንስ እና የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አራግቺ

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር የደረሰችው የመግባቢያ ሰነድ ይዘት በሚመለከታቸው የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የመጨረሻ ውሳኔ እንዳልተሰጠበት ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያላቸው የዜና ምንጮች ዘገቡ።

    ታስኒም የተባለው የዜና ወኪል ስማቸው ያልተገለጸ ጉዳዩን የሚያውቁ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ባለፉት ቀናት በማስፈራራት፣ በጫና እና በወታደራዊ እርምጃ እንዲሁም በኳታር አሸማጋዮች በኩል የኢራንን አቋም ለማስቀየር ሞክረው ነበር። ነገር ግን ኢራን የተደረጉትን አዳዲስ ለውጦች ለመቀበል አልፈቀደችም” ብለዋል።

    የዜና ወኪሉ ጨምሮም እንደገለጸው ከአሜሪካ ጋር መግባባት ላይ የተደረሰበት ሰነድ “በሚመለከታቸው የኢራን ተቋማት ተመርምሮ ተቀባይነትን ማግኘት አለበት፤ ነገር ግን እስከዚያው የሚነገሩ ግምቶች እና ዜናዎች ትክክለኛ አይሆኑም።”

    ሌላኛው የኢራን ዜና አገልግሎት ፋርስ አሜሪካ አንዳንድ ቅድመ ሁኔታዎቿን የተወች መሆኑን፣ ነገር ግን “ገና ምንም ዓይነት ስምምነት ላይ አልተደረሰም። ስዊትዘርላንድ ውስጥ ስምምነቱ ስለመፈረሙ ወይም ፊት ለፊት ስለሚደረግ ንግግር የሚወራው ተጨባጭ አይደለም” በማለት ዘግቧል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሐሙስ ማታ “የኢራን መንግሥት ባለሥልጣናት በእያንዳንዱ ነጥብ ላይ ውሳኔ እስከሚሰጡ ድረስ ስለፊርማው ሥነ ሥርዓት እና ቦታው መነጋገር የሚፈይደው ነገር የለም” ብለው ነበር።

    ነገር ግን የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ቀደም ብለው ከኢራን ጋር ከስምምነት መደረሱን በመግለጽ “ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት አብቅተናል” በማለት አሳውቀው ነበር።

    ፕሬዝዳንቱ በጽህፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት በጥቂት ቀናት ውስጥ ለስምምነቱ ፊርማ ምክትላቸው ጄ.ዲ ቫንስ ወደ አንድ የአውሮፓ ከተማ እንደሚሄዱ ገልጸዋል።

    በተጨማሪም የአሜሪካ ኃይሎች በደቡባዊ ኢራን የጣሉት የባሕር ላይ ዕገዳ ስምምነቱ እስኪቋጭ ድረስ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ መሆኑ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

  17. ታዋቂዋ ዘፋኝ አሪያና ግራንዴ የአሜሪካ መንግሥት ሙዚቃዋን ለፀረ ስደተኞች ፖሊሲው እንዳይጠቀም ጠየቀች

    አሪያና ግራንዴ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty

    የምስሉ መግለጫ, አሪያና ግራንዴ

    ታዋቂዋ አሜሪካዊት ዘፋኝ አሪያና ግራንዴ ሙዚቃዋ የአሜሪካን የስደተኞች ፖሊሲን ለማስተዋወቅ ጥቅም ላይ እንዳይውል የፕሬዝዳንቱን ጽህፈት ቤት ጠየቀች።

    በቲክቶክ ላይ በተጋራው ቪዲዮ ላይ የአሜሪካ የድንበር ጠባቂዎች ሰዎችን እጃቸውን በካቴና እያሰሩ ወደ እስር ቤት ሲወስዷቸው የአሪያና ግራንዴ “ጉድባይ” [ደህና ሁኑ] የሚለው ታዋቂ ዘፈን በማጀቢያነት ጥቅም ላይ ውሏል።

    የቪዲዮው ማብራሪያ “ደህና ሁኑ...ፕሬዝዳንት ትራምፕ በታሪክ በደንብ የሚጠበቅ ድንበር ፈጥረዋል” ይላል።

    አሪያና ግራንዴ ይህንን ቪዲዮ በተመለከተ "እባካችሁ ሙዚቃዬን ከዚህ ጭካኔ ከተሞላበት፣ ሰብአዊነት ከጎደለው ክፋት ጋር አታያይዙት” ስትል ጽፋለች።

    የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ አቢጌል ጃክሰን ለአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን በሰጠችው ምላሽ “በትክክልም ጭካኔ የሞላበት፣ ሰብአዊነት የጎደለው እና ክፉው ድርጊት ሕገወጥ ስደተኞች ንጹሃን አሜሪካውያንን መጉዳታቸው ወይም መግደላቸው ነው” ብላለች።

    ዋይት ሐውስ ቪዲዮውን ያጋራው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለቀጣይ ሁለት ዓመት ተኩል ለስደተኞች ተቆጣጣሪ ተቋማት የሚውል 70 ቢሊዮን ዶላር በጀት ካጸደቁ በኋላ ነው።

    አሪያና ግራንዴ በቪዲዮው ላይ ቅሬታዋን ካሰማች በኋላ የቪዲዮው ድምጽ እንዳይሰማ ሲደረግ የእሷ አስተያየትም ጠፍቷል።

    አሪያና ግራንዴ ሙዚቃቸው ለፕሬዝዳንት ትራምፕ የፖለቲካ አጀንዳ ማስተዋወቂያነት እንዳይውል ከጠየቁ ቁጥራቸው እየጨመረ ከመጣው የአርቲስቶች ዝርዝር ውስጥ ስሟ ተካትቷል።

    በተመሳሳይ ሙዚቃዋ የስደተኛ ተቆጣጣሪዎችን ሥራ በሚያሳይ ቪዲዮ ላይ ጥቅም ላይ የዋለባት ሌላኛዋ አሜሪካዊት ሙዚቀኛ ሳብሪና ካርፔንተር “እኔን እና ሙዚቃዎቼን ሰብአዊነት ለሌለው ዓላማችሁ ፈጽሞ አትጠቀሙ” ብላ ጽፋ ነበር።

    አባ፣ ሴሊን ዲዮን እና ቢዮንሴ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ድጋሚ ለመመረጥ ቅስቀሳ በሚያደርጉበት ጊዜ ሙዚቃዎቻቸውን እንዳይጠቀሙ ከጠየቁ ድምጻውያን መካከል ይገኙበታል።

  18. የትራምፕ አስተዳደር ኢራናውያን ስደተኞችን ወደ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ለመላክ ማቀዱ ተዘገበ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ኢራናውያን ስደተኞችን ወደ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ለመላክ ማቀዱን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    ሮይተርስ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸውን ባለሥልጣንን እና ሁለት ጠበቆችን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ የትራምፕ አስተዳደር በግጭት ወደምትናጠው አገር ኢራናውያን ስደተኞችን ለመላክ አቅደዋል።

    ኢራናውያን ስደተኞችን የሚወክሉት ጠበቃ ኤምሊ ትሩሰል እንደተናገሩት ወደ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ይላካሉ ከተባሉት መካከል ሁለት ሴቶች ይገኙበታል። ኢራናውያኑ ወደ ትውልድ አገራቸው ከተመለሱ እንግልት እና ስቅይት እንደሚጠብቃቸው ጠበቃቸው ተናግረዋል።

    ሮይተርስ እንደዘገበው በቅርቡ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፤ አሜሪካ የምታስወጣቸውን ስደተኞች ለመቀበል ከአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር ስምምነት ላይ ደርሷል።

    ስለ ጉዳዩ ሁለቱም ወገኖች አስተያየት አልሰጡም።

    ሮይተርስ ያነጋገራቸው ባለሥልጣን እንደተናገሩት በመጀመሪያው ጉዞ ከኢራናውያን በተጨማሪ ሶሪያውያን እና አፍጋኒስታናውያን የሆኑ 20 ስደተኞች የሚጓዙ ይሆናል።

    ከአሜሪካ የሚባረሩት ስደተኞች በሚቀጥለው ሳምንት መጨረሻ ገደማ ወደ አፍሪካዊቷ አገር እንደሚጓዙ ተናግረዋል።

    ከሚባረሩት ሰዎች መካከል ሕጋዊ መኖሪያ ለማግኘት አመልክተው ሳለ ተይዘው ከአሜሪካ እንዲባረሩ በኢሚግሬሽን ፍርድ ቤት የተወሰናባቸው ይገኛሉ።

    ስደተኞች ሲባረሩ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

  19. ከትራምፕ ንግግር በኋላ የነዳጅ ዋጋ ሲቀንስ፣ ኢራን ስምምነቱ ገና አልተቋጨም አለች

    ቴህራን ውስጥ የሚታይ የሕንጻ ላይ ምሥል

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት የሚያስቆም ስምምነት ላይ መደረሱን ሲያስታውቁ ኢራን ግን ገና መቋጫ ላይ አለመደረሱን ገለጸች።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚካሄደው ጦርነት የበለጠ ይባባሳል ተብሎ በተሰጋበት ጊዜ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ላይ እንደሚፈጸም የተናገሩትን ጥቃት ሰርዘው የመጀመሪያ ደረጃ ስምምነት ላይ መደረሱን ተናግረዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ለአገራቸው ቴሌቪዥን ከስምምነት ተደርሷል መባሉን “ግምታዊ” በማለት “ከመደምደሚያው ላይ እንዳልተደረሰ” ገልጸዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከዚህ ቀደምም ሁለቱ አገራት ጦርነቱን ወደሚያበቃ ስምምነት እየተቃረቡ መሆናቸውን በተደጋጋሚ ተናግረው እንደነበር ይታወሳል።

    ይህ የትራምፕ ንግግር ከተሰማ በኋላ ውጥረቱ በተባባሰባቸው ባለፉት ቀናት ጭማሪ እየሳየ የነበረው የዓለም ገበያ ዋጋ ከአራት በመቶ በላይ ቅናሽ በመሳየት በበርሜል ወደ 89 ዶላር ወርዷል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ በጽሕፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት "ኢራን ፈጽሞ የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንዳይኖራት የሚያደርግ ስምምነት ላይ ደርሰናል፤ ይህንን ለማሳካት ስንል ነበር በዚህ ሁሉ ውስጥ ያለፍነው። በጣም ትልቅ ስምምነት ነው” ብለዋል።

    ጨምረውም የስምምነቱ ሰነድ ተዘጋጅቶ ሲያበቃ “በጣም በፍጥነት” ሁለቱ አገራት “ምናልባትም ፊርማው አውሮፓ ውስጥ” ይካሄዳል ብለዋል።

    በጦርነቱ ምክንያት የተዘጋው ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ መስመር ሆርሙዝም “ስምምነቱ ሲፈረም ወዲያውኑ ይከፈታል” በማለት በጉዳዩ ላይ ከእስራኤል እና ከመካከለኛው ምሥራቅ አጋር አገራት ጋር መነጋገራቸውን እነሱም “ደስተኛ” መሆናቸውን ተናግረዋል።

    ለውጤቱ ለትራምፕ ያላቸውን አድናቆት የገለጹት የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ስምምነቱ “[የኢራንን] የዳበረ ዩራኒየም ማስወገድ፣ የዩራኒየም ማበልጸጊያ ተቋማትን ማውደም፣ የሚሳዔል ምርቷን መገደብ እና በቀጣናው ላሉ ሽብርተኛ ቡድኖች ድጋፏን ማቆም” የሚሉ እንደሚገኙበት ገልጸዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እንዳሉት ደግሞ የሚፈረመው የመግባቢያ ሰነድ “ቢጠናቀቅም” አሜሪካ “ከልክ ያለፉ እና አዳዲስ ጥያቄዎችን እያቀረበች ነው” በማለት ኢራን ካስቀመጠችው “ቀይ መስመር ፈቀቅ እንደማትል” አስታውቀዋል።

  20. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን ላይ የሚደርሰው ጥቃት ‘እንደቆመ’ አስታወቁ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ላይ የሚሰነዘረው ጥቃት ‘እንደተገታ’ አስታወቁ።

    ከኢራን ጋር የሚደረገው ውይይት መሻሻል እንዳሳየ እና ከስምምነት ሊደረስ እንደሚችልም ገልጸዋል።

    ትራምፕ ትናንት ሐሙስ ኢራንን “ክፉኛ እንመታለን” ብለው ቢዝቱም፤ ሊያደርሱት የነበረውን ጥቃት ለመሰረዝ መወሰናቸውን ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ኻርግ ደሴት ላይ ጥቃት እንደሚፈጸም አስጠንቅቀው ነበር።

    ከኢራን ጋር የሚፈረመው የመግባቢያ ሰነድ “የመጨረሻ ደረጃ” ላይ መድረሱን ጠቅሰው በዚህ ሳምንት ስምምነቱ ሊገባደድ እንደሚችል አስረድተዋል። ስምምነቱ የሚፈረመው አውሮፓ ውስጥ እንደሚሆን ጠቁመዋል።

    ስምምነቱ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳይኖራት የሚያግድ እንዲሁም በአፋጣኝ የሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲከፈት የሚያስገድድ እንደሚሆን ትራምፕ አስረግጠው ተናግረዋል።

    ትራምፕ ይህንን ቢሉም የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ስምምነት ላይ ለመድረስ አለመቃረባቸውን አስታውቀዋል።

    አሜሪካ በድርድሩ “ከልክ ያለፈ ጥያቄ” እያቀረበች እንደሆነም ጠቅሰዋል።

    ኳታር ሁለቱን አገራት ለማሸማገል ጥረት እያደረገች እንደሆነ ተጠቁሟል።

    ትራምፕ ኢራን ላይ ጥቃት እንደማይፈጸም መግለጻቸውን ተከትሎ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ ቀንሷል።