የኪባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የእስራኤል ድብደባን እንዲያስቆም ጠየቁ

የፎቶው ባለመብት, EPA
የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም ከፍተኛ የአየር ድብደባ ከተፈጸመ በኋላ "የሊባኖስ ወዳጆች በሙሉ" የእስራኤልን ወታደራዊ እርምጃ "በሚችሉት መንገድ ሁሉ" እንዲያስቆሙ ተማጸኑ።
ናዋፍ ሳላም በኤክስ ገጻቸው ላይ "እስራኤል በሊባኖስ በተለይም በዋና ከተማዋ ቤይሩት ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎች ያልታጠቁ ሰላማዊ ሰዎችን ሕይወት የቀጠፈ በሕዝብ በተጨናነቁ የመኖሪያ ሰፈሮች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች" ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጥሪ ያቀረቡት የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት በሄዝቦላህ ላይ ዘመቻ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በተለየ በመላው ሊባኖስ ዛሬ “መጠነ ሰፊ ድብደባ” መፈጸሙን ካስታወቀ በኋላ ነው።
ሳላም እንደሚሉት የአይዲኤፍ ጥቃቶች ለዓለም አቀፍ ሕግ "ፍፁም ቸልተኝነት" አሳይተዋል።
አክለውም "እናም ሁሉም የሊባኖስ ወዳጆች እነዚህን ጥቃቶች በሁሉም መንገዶች ለማስቆም እንዲረዱን ጥሪ እናቀርባለን" ብለዋል።
ሊባኖን 24 የተባለ የአረብኛ ዜና ወኪል በበኩሉ በኤክስ ገጹ ላይ በሊባኖስ የሚገኙ ሆስፒታሎች በተጎጂዎች መጨናነቃቸውን አጋርቷል።
የሊባኖስ ጤና ሚኒስትር በበኩሉ ዜጎች አውራ መንገዶችን ለአምቡላንሶች እንዲለቅቁ ጠይቋል።
የሄዝቦላህ ደጋፊ የሆነው አል ማናር ቴሌቪዥን ጣቢያ ደግሞ እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ ቤይሩት በፈጸመችው ጥቃት በርካቶች መሞታቸውን እና መጎዳታቸውን በቴሌግራም ገጹ ላይ ጽፏል።
ኤልቢሲአይ የተባለ የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን በኤክስ ገጹ ላይ የአገሪቱን ጤና ሚኒስቴር ጠቅሶ በእስራኤል ጥቃት መቶዎች መሞታቸውን እና መጎዳታቸውን አጋርቷል።
በመንግሥት የሚመራው የአገሪቱ የዜና ወኪል በበኩሉ በደቡባዊ ሊባኖስ አድሉን ከተማ በአንድ ቤት ላይ በተፈጸመ ጥቃት ሦስት ሴቶች መገደላቸውን ዘግቧል።
አሜሪካ እና ኢራን ለሁለት ሳምንት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ሲደርሱ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ይህ “ሊባኖስን አያካትትም” ብለዋል።


















