ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና የኤም- 23 አማፂያን በሰላም ንግግር ማዕቀፎች ላይ ተስማሙ
የዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ መንግሥት እና በሩዋንዳ የሚደገፈው የኤም 23 አማፂ ቡድን የሰላም ድርድር ፍኖተ ካርታ ላይ ከስምምነት ደረሱ።
በስዊትዘርላንድ ለአምስት ቀናት የተወያዩት ሁለቱ ወገኖች በጋራ ባወጡት መግለጫ “ሁሉን አቀፍ ሰላም ለማምጣት እና ግጭት ለመፍታት የሚያስችል ድርድር ለማድረግ” እንዲሁም የተኩስ አቁሙን ስምምነቱን አፈጻጸም ለመከታተል የሚያስችል አካል ለማቋቋም ቃል መግባታቸውን ተናግረዋል።
ፍኖተ ካርታው በ2025 በአሜሪካ አስተባባሪነት በተፈረመው የሰላም ማዕቀፍ ሥር ለሚደረጉ ውይይቶች የጊዜ ሰሌዳ ያስቀምጣል።
ነገር ግን በኤም 23 ላይ የተጣሉ ማዕቀቦች፣ የታሳሪዎች አለመፈታት እና የፖለቲካ ማሻሻያዎች የሚደረጉበትን ጊዜ ጨምሮ በርከት ያሉ ጉዳዮች አሁንም በቡድኖቹ መካከል ላለመግባባት ምክንያት ናቸው።
በድርድሩ ላይ ኤም 23፣ የዲሞክራቲክ ኮንጎ መንግሥት፣ ኳታር፣ አሜሪካ፣ የቶጎ ሪፐብሊክ፣ የአፍሪካ ኅብረት እና አስተናጋጇ ስዊትዘርላንድ ተሳትፈዋል።
"ተፈላሚ ወገኖች የዶሃ ማዕቀፍ ስምምነትን ተከትሎ የተጣለባቸውን ግዴታዎችና ኃላፊነቶችን ተግባራዊ ለማድረግ የገጠሙ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የሚያስችል አካል ለማቋቋም ተስማምተዋል።" ሲል መግለጫው አክሏል።
ግጭቱ በዲሞክራቲክ ኮንጎ እና በአጎራባች ሩዋንዳ መካከል ካለው ውጥረት ጋር በቅርበት የተያያዘ ነው።
ሩዋንዳ የፀጥታ ስጋት እንደሆነ የምትቆጥረውን ኤፍዲኤልአር የተባለውን ነፃ አውጪ ኃይል ዲሞክራቲክ ኮንጎ ማፍረስ እንዳልቻለች ገልጻለች።
ዲሞክራቲክ ኮንጎ ታጣቂ ቡድኑን ኤፍዲኤልአርን እንደማትደግፍ አስተባብላ ሩዋንዳም ኤም-23ን በወታደሮችና በጦር መሳሪያዎች እንደምትደግፍ ትከሳለች።
በጥር 2025 ኤም23 ጎማን እና ሁለት የአየር ማረፊያዎችን ጨምሮ ሲቆጣጠር ግጭቱ ተባብሶ ነበር።
በአስርት ዓመታት በተካሄደው ጦርነት በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የተገደሉ ሲሆን በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሲቪሎች ከቤታቸው ተፈናቅለዋል።
ምሥራቃዊ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ለዓለም አቀፍ የኤሌክትሮኒክ ኢንዱስትሪዎች አስፈላጊ በሆኑ ኮልታን እና ሌሎች ማዕድኖች የበለፀገች ናት።