ቀጥታ, ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈጸም "እንዳይጣደፉ" አሳሰቡ

አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያደርጉት ድርድር ወደ ማጠናቀቂያው እንደተቃረበ መነገሩን ተከትሎ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸው “በጥድፊያ" ከኢራን ጋር "ስምምነት እንዳይፈጽሙ” አዘዙ። በሁለቱ አገራት ንግግር እየተደረገበት ያለው የስምምነት ዕቅድ ከያዛቸው ነጥቦች መከካከል፤ የተኩስ አቁሙን ለ60 ቀናት ማራዘም፣ የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መክፈት እንዲሁም የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም በተመለከተ ተጨማሪ ድርድር ማካሄድ የሚሉት ይገኙበታል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይደረሳል በሚል ተስፋ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ አሳየ

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይፈረማል የሚል ተስፋ በስፋት በመታየቱ የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ቀነሰ። የእስያ የአክሲዮን ገበያዎች ላይም ጭማሪ ታይቷል።

    ቅዳሜ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቴህራን ጋር የሰላም ስምምነቱ ነጥቦች "በአብዛኛው ድርድር ተደርጎባቸዋል" በማለት ዝርዝሩን ይፋ ሳያደርጉ ቀርተዋል።

    ሁለቱ አገራት በበርካታ ጉዳዮች ላይ መስማማታቸው ሲገለጽ ቢቆይም ትራምፕ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈራረም እንዳይጣደፉ አሳስበዋል።

    ሰኞ ጠዋት በእስያ ገበያ ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ 5.5 በመቶ ቅናሽ ያሳየ ሲሆን በአሜሪካ ደግሞ የ5.8 በመቶ ቀንሶ 90.99 ዶላር ተሸጧል።

    ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገው ድርድር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ማስከፈትን የሚያካትት ነው ያሉ ሲሆን ይህም ለወራት መንቀሳቀሻ አጥተው የቆሙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በነጻነት እንዲጓዙ ያስችላል ተብሎ ነበር።

    ጠባቡ የባሕር መተላለፊያ የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት ሲሆን ከየካቲት 21 2018 ዓ.ም. በኋላ ተዘግቷል።

    ቅዳሜ ዕለት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ከሳዑዲ አረቢያ፣ ከዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ፣ ኳታር ጋር “በሰላም ስምምነቱ የመግባቢያ ሰነድ” ዙሪያ “ጥሩ ውይይት” ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

  2. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈጸም "እንዳይጣደፉ" አሳሰቡ

    አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያደርጉት ድርድር ወደ ማጠናቀቂያው እንደተቃረበ መነገሩን ተከትሎ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸው ከኢራን ጋር “ተጣድፈው ወደ ስምምነት እንዳይገቡ” አዘዙ።

    በሁለቱ አገራት ንግግር እየተደረገበት ያለው የስምምነት ዕቅድ ከያዛቸው ነጥቦች መከካከል የተኩስ አቁሙን ለ60 ቀናት ማራዘም፣ የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መክፈት እንዲሁም የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም በተመለከተ ተጨማሪ ድርድር ማካሄድ የሚሉት ይገኙበታል።

    ትራምፕ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ንግግሩ “ገንቢ” በሆነ ሁኔታ እየተካሄዱ መሆኑን ቢገልጹም፤ አክለው ግን “ሁለቱም ወገኖች ጊዜያቸውን መውሰድ እና በትክክል ማከናወን አለባቸው” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ቅዳሜ ዕለት ስምምነቱ “በአብዛኛው ድርድር እንደተደረገበት” መገናራቸው ስምምነት ይፋ መደረጉ አይቀሬ ነው የሚል ግምት ፈጥሮ ነበር።

    የኢራን ባለሥልጣናትም ተመሳሳይ ሀሳብ አመልክተው ነበር። የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ሁለቱ ወገኖች ስምምነት ላይ ለመድረስ “እጅግ ቅርብ እና እጅግ ሩቅ” ናቸው ብለው ነበር።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡ ከሆነ ድርድር የሚካሄድበት እቅድ የመጨረሻው ስምምነት አይደለም። ይልቁንም ሁለቱ አገራት የተወሰኑ አጨቃጫቂ ጉዳዮች በኋላ ድርድር እንዲካሄድባቸው እንደሚፈቅድ ዘግበዋል።

    ኢራን ላይ የተጣለው ማዕቀብ የሚነሳበት መጠን እና ጊዜ፣ የታገደውን የኢራን ገንዘብን የማስለቀቅ ጉዳይ እንዲሁም አሜሪካ የቴህራንን የኒውክሌር ፍላጎት ለመገደብ ያላት ፍላጎት ለበኋላ ድርድር ከሚተዉ ነጥቦች መካከል ናቸው።

    ይህ የስምምነት ዕቅድ ሪፐብሊካኖችን ለሁለት የከፈለ ሲሆን የተወሰኑት ኢራን ላይ ለዘብተኛ አቋም የያዘ እንደሆነ በይፋ እየተናገሩ ነው።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ባጋሩት ልጥፍ፤ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ ልትሰራ እንደማትችል “መረዳት እንዳለባት” በአጽንኦት አንስተዋል። ቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ ዓላማ እንደሚውል በተደጋጋሚ ስትገልጽ ቆይታለች።

    አንዳንድ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ከኢራን ጋር በሚደረሰው ስምምነት አማካኝነት ኢራን የበለጸገ ዩራኒየሟን አሳልፋ እንደምትሰጥ ዘግበዋል።

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ለአገሪቱ ቴሌቪዥን በሰጡት ቃለ መጠይቅ ቴህራን “ፍላጎቷ የኒውክሌር መሣሪያ እንዳልሆነ ለዓለም ለማረጋገጥ” ዝግጁ እንደሆነች ተናግረዋል።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው በድርድሩ “ጉልህ” መሻሻል ቢታይም፤ ሂደቱ “የመጨረሻ ደረጃ እንዳልደረሰ” ገልጸው ነበር።