ፕሬዝዳንት ሙሴቬኒ በልጃቸው የሚመራ የፀረ ሙስና ዘመቻ በባለሥልጣናት ላይ ጀመሩ
ፕሬዝዳንት ሙሴቬኒ የኡጋንዳ ጦር ሠራዊት አዛዥ በሆነው በልጃቸው የሚመራ በአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ላይ የፀረ ሙስና ዘመቻ መጀመራቸው ተዘገበ።
በዚህም የተነሳ ካምፓላ የሚገኘው የተሰናባቿ የአገሪቱ ፓርላማ አፈ ጉባዔ መኖሪያ ቤት በኡጋንዳ የደኅንነት ኃይሎች ተፈትሾ ሮልስ ሮይስ እና ሬንጅ ሮቨርን ጨምሮ ቅንጡ መኪኖች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተነግሯል።
የአገሪቱ ጦር አዛዥ እና የፕሬዝዳንቱ ልጅ የሆኑት ሙሁዚ ካይኔሩጋባ አባታቸው ኡጋንዳ ውስጥ የሚገኝ ማንኛውንም ሰው በቁጥጥር ስር የማዋል ሥልጣን እንደሰጧቸው ተናግረዋል።
የፀረ ሙስና ዘመቻው ለአራት አስርት ዓመታት ኡጋንዳን እየመሩ ባሉት በፕሬዝዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ትዕዛዝ የሚካሄድ ሳይሆን እንደማይቀር ይታመናል።
ቤታቸው የተፈተሸው አፈ ጉባዔዋ የፕሬዝዳንቱ የቅርብ ሰው ተደርገው ይታዩ የነበረ ሲሆን ለረዥም ጊዜ ስማቸው ከሙስና ጋር ሲነሳ ቆይቷል። በዚህም በብሪታኒያ እና በአሜሪካ ማዕቀቦች ተጥሎባቸዋል።
አሁን ከባለሥልጣኗ ቤት የተያዙት ውድ ንብረቶች በጨረታ ተሽጠው ገንዘቡ ለሕዝብ እንደሚመለስ የጦሩ አዛዥ ተናግረዋል።
በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በሚያጋሯቸው መልዕክቶች አነጋጋሪ የሆኑት የፕሬዝዳንቱ ልጅ ከሰሞኑ ባሠራጩት ጽሁፍ በዋና ከተማዋ ባሉ መንገዶች ላይ ጉድለት ከተገኘ የግንባታውን ኮንትራት የወሰዱትን ሰዎች አንገታቸውን እንደሚቀሉ አስጠንቅቀዋል።