ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ሊያልፉ የነበሩ ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን መመለሷ ተዘገበ
ኢራን በሆርሙዝ በኩል የሚደረግ ጉዞ ላይ ትናንት በድጋሚ የጣለችው እገዳ ቀጥሎ፤ የአገሪቱ “ጦር ኃይሎች በዛሬው ዕለት ሁለት ተጨማሪ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች” በወሽመጡ እንዳያልፉ መመለሳቸውን ታስኒም የዜና ወኪል ዘገበ።
ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ግንኙነት ያለው የዜና ወኪል ዘገባ እንደሚያሳየው፤ ሁለቱ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች “የቦትስዋና እና አንጎላ ባንዲራን አድርገው እየቀዘፉ” ነበር።
በሆርሙዝ በኩል ለማለፍ ፈልገው የነበረ ቢሆንም “የኢራን ጦር ኃይሎች በወሰዱት ጊዜውን የጠበቀ እርምጃ አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ እና እንዲያፈገፍጉ” መደረጉንም ገልጿል።
ኢራን ከጦርነቱ መጀመር አንስቶ ዘግታው የነበረውን ሆርሙዝ አርብ ዕለት ከፍታ የነበረ ቢሆንም አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ እገዳ መጣሏን እንደምትቀጥል መግለጿን ተከትሎ ወሽመጡን በድጋሚ ዘግታለች።
በትናንናው ዕለት በድጋሚ እገዳው ከተጣለ በኋላ ለማለፍ የሞከሩ መርከቦች ከኢራን ኃይሎች ተኩስ እንደተከፈተባቸው ገልጸዋል።
የመርከቦች ጉዞ መከታተያ ድረ ገጽ የሆነው ‘ማሪን ትራፊክ’ መረጃ እንደሚያመለክተው አንድም መርከብ በወሽመጡ በኩል አላለፈም።
በርካታ መርከቦች በኦማን እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የባሕር ዳርቻዎች መልህቃቸው ጥለው እንደሚገኙም መረጃው ያሳያል።
ትናንት በወሳኙ መተላለፊያ በኩል የተወሰነ ጉዞ ተስተውሎ የነበረ ቢሆንም ኢራን ወሽመጡን መዝጋቷን ካስታወቀች በኋላ በከፍተኛ መጠን ቀንሷል።