ትራምፕ ኢራን ላይ ያላቸው ትዕግሥት እየተሟጠጠ መሆኑን ተናገሩ

የፎቶው ባለመብት, Fox News
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቻይናው መሪ ዢ ጂንፒንግ ጋር ከተነጋገሩ በኋላ ኢራን ላይ ያላቸው ትዕግሥት እየተሟጠጠ መሆኑን ተናገሩ።
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ሐሙስ ዕለት ከቻይናው መሪ ዢ ጂንፒንግ ጋር ስለ ኢራን ጦርነት ከተነጋገሩ በኋላ ለፎክስ ኒውስ በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ ትዕግሥታቸው እየተሟጠጠ መሆኑን ነው የገለጹት።
በትናንትናው ዕለት ከተባበሩት አረብ ኤሜሪትስ የባሕር ዳርቻ ወጣ ብሎ በሚገኝ ስፍራ የኢራን ወታደሮች መርከብን ማገታቸው ተሰምቷል።
ዋይት ሐውስ ትራምፕ እና ዢ በውይይታቸው ወቅት የሆርሙዝ ወሽመጥ ክፍት እንዲሆን መስማማታቸውን ገልጿል።
እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21 2018 ዓ.ም. ጦርነት ከከፈቱባት በኋላ ኢራን የአጸፋ እርምጃ በመውሰድ የሆርሙዝ ወሽመጥን ዘግታለች።
ይህም የዓለም የነዳጅ ዘይት እና ጋዝ ፍሰትን እንዲሁም ንግድን አስተጓጉሏል።
ቻይና የኢራን የቅርብ አጋር ስትሆን ከፍተኛ የሆነ የነዳጅ ዘይትም የምትገዛው ከእርሷ ነው።
አሜሪካ በቴህራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ባለፈው ወር ያቋረጠችው ኢዝላማባድ ካደራደረች በኋላ ሲሆን ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ የመርከብ እንቅስቃሴዎችን ግን ሙሉ በሙሉ አግዳለች።
ኢራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን ለማቋረጥ እና የበለጸገው ዩራኒየሟን ለማስረከብ ባለማስማማቷ በሁለቱ አገራት መካከል የተጀመረው ንግግር ተቋርጧል።
ትራምፕ ከፎክስ ኒውስ ጋር በነበራቸው ቃለምልልስ ወቅት “ከዚህ በላይ ትዕግሥት አይኖረኝም” ብለዋል።
አክለውም “መስማማት አለባቸው” ሲሉ ተደምጠዋል።
ኢራን ያከማቸችው የበለጸገ ዩራኒየም ከደህንነት አንጻር ያን ያህል አሳሳቢ እንደማይሆን ገልጸው ለሕዝብ ግንኙነት ሥራ ግን በአሜሪካ ቁጥጥር ስር መሆን እንዳለበት ጠቅሰዋል።
“ከሕዝብ ግንኙነት ሥራ በስተቀር አስፈላጊ የሚሆን አይመስለኝም” ሲሉ በቃለ ምልልሱ ላይ ተናግረዋል።
“በእኔ ቁጥጥር ሥር ቢኖር የበለጠ ጥሩ ይሰማኛል። ነገር ግን እንደማስበው ከሌላ ነገር ይልቅ የበለጠ የሕዝብ ግንኙነት ሥራ ነው።”






















