ኢራን ጎረቤቶቿ ላይ ሥጋት የመሆን አቅሟ በከፍተኛ መጠን መውረዱን የአሜሪካ ወታደራዊ አዛዥ ተናገሩ
ኢራን ጎረቤቶቿን እና የአሜሪካ ጥቅም ያለባቸው ስፍራዎችን ስጋት ውስጥ ለመክተት ያላት አቅም በዋሽንግተን ጥቃት ምክንያት በከፍተኛ መጠን እንደቀነሰ የአሜሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ አዛዥ መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ።
የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ አዛዡ አድሚራል ብራድ ኩፐር፤ በተፈጸሙት ጥቃቶች ምክንያት የኢራን የመከላከያ ኢንዱስትሪ 90 በመቶ ወደ ኋላ መመለሱን ገልጸዋል።
ወታደራዊ አዛዡ ይህንን ያሉት የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን የአሜሪካ የስለላ መረጃን መሠረት አድርገው ባወጡት ዘገባ የኢራን የሚሳዔል ክምችት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሚገልጹት ደረጃ ጉዳት እንዳልደረሰበት ከዘገቡ በኋላ ነው።
የአሜሪካው ጋዜጣ ዋሽንግተን ፖስት፤ ኢራን አሁንም ከፍተኛ የባለስቲክ ሚሳዔል አቅም እንዳላት የሲአይኤ ሪፖርትን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ አስነብቦ ነበር።
ኢራን ከጦርነቱ በፊት ከነበሯት ተንቀሳቃሽ ሚሳዔል ማስወንጨፊያዎች ውስጥ 75 በመቶውን እንዲሁም ከሚሳዔል ክምችቷ 70 በመቶውን አሁንም እንደያዘች ተገልጿል።
የዜና ወኪሉ ሮይተርስም፤ ኢራን ከምድር ስር ባሉ ተቋማት ከፍተኛ የሚሳዔል እና የድሮን ክምችት እንዳላት ዘግቦ ነበር።
ሮይተርስ ዛሬ ያወጣው ዘገባ እንደሚያሳየው፤ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ አዛዡ አድሚራል ብራድ ኩፐር እነዚህ ዘገባዎችን በቀጥታ ጠቅሰው ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበዋል።
ይሁን እንጂ በሴኔት ኮሚቴ በነበረው ስብሰባ ላይ “ኢራን በከፍተኛ ደረጃ የወረደች ስጋት ነን። ከአሁን ወዲህም ከዚህ ቀደም ማድረግ ይችሉት በነበረው መንገድ፤ በሁሉም ዘርፍ ቀጣናዊ አጋሮች ወይም አሜሪካ ላይ ስጋት አይጥሉም” ብለዋል።
ወራደራዊ አዛዡ አክለውም ከአሁን በኋላ ኢራን በቀጣናው የሚገኙ ዋነኛ አጋሮቿ ለሆኑት ሄዝቦላህ፣ ሁቲ እና ሐማስ መሣሪያ እንዲሁም ሌሎች ሀብቶችን ማስተላለፍ እንደማትችል መናገራቸውን ዘገባው ያሳያል።
“እነዚያ የማስተላለፊያ መንገዶች እና ዘዴዎች ተቆርጠዋል” ብለዋል።